EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Thursday 2 March 2017

የዓድዋ ጀግኖችን ጽናት ተላብሰን ህዳሴያችንን ለማሳካት እንረባረብ!

(በኤፊ ሰውነት)
አድዋ ሲነሳ አስቀድሞ ወደ አዕምሮ የሚመጣው እውነታ አውሮጳውያን ኃያላን በበርሊን ያደረጉት ‹‹አፍሪቃን የመቀራመት›› ሴራ ይመስለኛል፡፡ ቅኝ ገዥዎች ድንበር ጥሰው፤ የአገር ሉዓላዊነት ተዳፍረው አፍሪካን ሲቀረማመቱ ኢትዮጵያ እና ሶማሊያ የጣሊያን ድርሻ እንዲሆኑ ተወሰነ፡፡ የመጀመሪያው የጣሊያን ጦር በባሕረ ነጋሽ (የአሁኗ ኤርትራ) በኩል ሲመጣ የወቅቱ የባሕረ ነጋሽ ገዢ የነበሩት የራስ አሉላ አባ ነጋ ሠራዊት የጣሊያንን ሠራዊት ዶጋሊ ላይ በተደረገ ፍልሚያ ድል ነስቶ አገር ማለት ክብር፣ አገር ማለት የማይደፈር ህዝብ መሆኑን በተግባር አሳይቶ መለሳቸው፡፡ ያኔ ሁኔታው አልዋጥ ያለው የጣሊያን ፓርላማ ተሰብስቦ ተጨማሪ 5000 ወታደር የያዘ ሠራዊት በመላክ ኢትዮጵያን በኃይል ለማንበርከክ ወሰነ፡፡

ታሪክ እንደሚያስረዳን ጣሊያን እንደሌሎች አምባገነን የአውሮፓ አገራት ሁሉ ኢትዮጲያን በቅኝ ግዛት ስር ለማድረግ ውጫሌ ላይ ከኢትዮጵያ ጋር በተወካይዋ የውጫሌ ውል የሚባለውን ተዋዋለች፡፡ የውሉ አንቀፅ 17 የአማርኛ እና የጣልያንኛ ትርጓሜው እንዲለያይም ተደረገ፡፡ የጣሊያን መንግስት ኢትዮጵያን በጣሊያን ሞግዚት አስተዳደር ስር መሆኗን በሚያመለክት መልኩ በመቅረፅ የአውሮፓ መንግስታት ጭምር እንዲያውቁት አደረገ፡፡ 
የሆነው ሆኖ በኢትዮጵያ በኩል በውሉ አንቀጽ 17 ላይ ጥያቄ ተነሳ፤ የጣሊያን መንግስት ደግሞ በአንቀፁ ላይ ጥያቄ ማንሳትን እንደውርደት በመቁጠሩ በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት አወጀ፡፡ መቼም ቢሆን ለውጭ ወራሪ ሃይል የማይንበረከከው የኢትዮጵያ ህዝብም የታወጀበትን ጦርነት ለመመከት ከዳር እስከ ዳር ነቅሎ ተነሳ፡፡ የአድዋ ጦርነት የካቲት 23 ቀን 1888 . በይፋ ተጀመረ፡፡ የኢትዮጵያ ጀግኖች በመሳሪያ የተደራጀውን የጣሊያንን ጦር ተፋለሙት፡፡ የጣሊያን ወታደሮች የኢትዮጵያ ጦር የሚፈፅመው ወኔ የተሞላበት ድርጊት እያስበረገጋቸው በመሸሻቸው የኢትዮጵያ የበላይነት በግልፅ በታየበት ጦርነት የጣሊያን ጦር ድል ተመታ፡፡ የካቲት 23 ቀን 1888 . ከጣሊያን ጋር በተካሄደው ጦርነት ጀግኖች አባቶቻችን እንደዛሬው ዘመናዊ ትጥቅ ሳይኖር፣ በባዶ እግራቸው አድዋ ዘምተው የጣሊያንን ጦር ድል በማድረግ ለአፍሪካውያን ኩራት የሆነ ድል ማስመዝገብ ቻሉ፡፡
የአድዋ ድል የቅኝ ገዥዎችን ቅስም የሰበረ፤ ጣሊያንን የሽንፈት ካባ ያከናነበ፤ የኢትዮጵያውያን ጀግንነት በምድረ አውሮፓም እንደተአምር እንዲወራ፣ ስማችን ከፍ ብሎ እንዲጠራ ያስቻለ ድል ሆነ፡፡ ይህ ድል ሌሎች የአፍሪካ ሀገራት እስከ 1960ዎቹ በቅኝ ግዛት ሲማቀቁ፤ ሲበዘበዙ፤ ሲጨቆኑ እኛ ግን ከባርነት ቀንበር ነፃ እንድንሆን አስችሎናል፡፡ በርካታ አፍሪካውያን በነጮች ቅኝ ግዛት ስር ወድቀው መራራውን ጊዜ በሚገፉበት በዚያን ዘመን እምቢ ለባርነት! እምቢኝ ለግዞት! ያሉት ጀግኖች አባቶቻችን የቅኝ ገዢዎችን ቅስም በመስበር አገራችን በጠላት ወረራ የማትደፈር ክብርት ሀገር መሆኗን አስረግጠው መልዕክት ያስተላለፉበት፣ ለአፍሪካውያንም ኩራት የሆኑበትን ድል የተጎናፀፉበት በመሆኑ ድሉ የእኛ ብቻ ሳይሆን የመላ ጥቁር ህዝቦች ድል እንደሆነ የታሪክ ተመራማሪዎች አስምረውበታል፡፡ ታፍራና ተከብራ የኖረችው አገራችን የአፍሪካ አንድነት ድርጅትን በማቋቋም ሂደት ውስጥም ግንባር ቀደም ተሳታፊ በመሆን ለሌሎች ነጻ መውጣት ጭምር የላቀ አስተዋፆ አበርክታለች፡፡

ዛሬ ግዞተኛ ሊያደርግን ጦር የሚሰብቅብን የውጭ ወራሪ ሃይል የለም፡፡ ዋናው ጠላታችን ድህነት ነው፡፡ በመቻቻልና በመተባበር መንፈስ ውስጥ ሆነን ድል ለማድረግ የምንተጋውም ድህነትንና ኋላ ቀርነትን ነው፡፡ ስለሆነም የዛሬው ትውልድ የአባቶቹን ፅናት በመላበስ በመለወጥ ላይ ያለችውን አገራችንን ወደ ተሻለ የዕድገት ምዕራፍ በማድረስ ጀግኖች አባቶቹ የፈጸሙትን አኩሪ ታሪክ በድህነት ላይ ሊደግም ይገባዋል፡፡ ለዚህም ነው 121ኛው የአድዋ ድል በዓል “የአድዋ ድል ብዝሃነትን ላከበረችው ኢትዮጵያ ድህነትን ለማሸመች የሚያስችል ህያው አብነት ነው!” በሚል መሪ ቃል የተከበረው፡፡

No comments:

Post a Comment