EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Saturday, 26 March 2016

ዓለምም እንደ ኢትዮጵያ የብዙህነት መናኸሪያ ነች!!


                                                                          ከታጋይ ሓዱሽ ካሡ
እ.አ.አ. ከ1990ዎቹ ጀምሮ ዓለም “አንድ መንደር” ሆናለች የሚል አባባል የሚደመጥባት መሆኑ የተለመደ ሆኗል፡፡ አባባሉ ከግሎባላይዜሽን መከሰት ጀምሮ በአራቱም የዓለም አቅጣጫ ያሉ ህዝቦች ቋንቋ ሆኗል ቢባል ማጋነን አይሆንም፡፡ “ዓለም አንድ መንደር” ሆናለች የሚባለው፣ በኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ስለተሳሰረችና የምትመራው በኢንፎርሜሽንና  በዕውቀት ስለሆነ ነው፡፡ ይኸውም በምዕራቡ የዓለም አቅጣጫ የተከሰተ አንድ ጉዳይ በማይክሮ ሴኮንዶች ውስጥ በምሥራቁ ዓለም እንደ ይሠራጫል፤ በተመሳሳይ በምስራቁ የተሰማ ምዕራቡ ጋር ሲደርስ ፋታ የለውም፡፡

የዓለም የግብይት ሥርዓት የሚከናወነውም በኢንተርኔት ነው፡፡ በመሆኑም ከፍተኛ ውድድር ውስጥ ባለችው ዓለማችን መኖር የሚቻለው ጥራትና መጠን ባለው ምርትና አገልግሎት በማቅረብ ብቻ ሳይሆን፣ ከሁሉም በፊት የፈጣን ኢንፎርሜሽንና ዕውቀት ባለቤት መሆን ግዴታ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ከዚህ አኳያ “ዓለም አንድ መንደር” ሆናለች የሚለው አባባል የሚያከራክር ሳይሆን ዕውነታውን የሚገልፅ ነው፡፡
በእርግጥ ዓለም የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ኔትዎርክ በፈጠረው ምቹ ሁኔታ የተነሳ እንደ ድር የተሳሰረ የምርትና የአገልግሎት ልውውጥ በማድረግ ላይ ነች፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ወቅት ከ7.6 ቢልዮን በላይ ህዝቦች በማህፀንዋ የያዘችው ዓለማችን  “አንድ መንደር” ሆናለች የሚለው መጠሪያ ብቻ ይገልፃታል ወይ?! የሚል ጥያቄ ቢነሳ በምላሹ አይደለም የሚል መከራከሪያ የሚያቀርብ ሰው አይጠፋም፡፡ እንዴትና ለምን ቢባል በቀላሉ ከሃብት ክፍፍል አኳያ እንኳን ብናይ፣ ከዓለማችን ህዝብ አንድ ከመቶ/1%/ የሚሆኑት ብቻ ጥቂት ባለሃብቶች የዓለምን ሃብት ተቆጣጥረው የተንደላቀቀ ኑሮ የሚኖሩባት ሆናለች፡፡ በአንፃሩ ዘጠና ዘጠኝ ከመቶ/99%/፣ የዓለም ህዝቦች፣ የሚበዙት የሚላስ የሚቀመስ የሌላቸው፣ የተቀሩት ደግሞ ካገኙ በቀን ሁለት ጊዜ አልያም አንድ ጊዜ ብቻ እህል ውሃ ብለው የሚኖሩባት ነች፡፡ ምድራችን ከቆዳ ቀለም አኳያም ጥቁር፣ የቀይ ዳማ፣ ብጫ፣ ቀይና ነጭ ቀለም ያሉዋቸው ህዝቦች መኖሪያ ነች፡፡

        ዓለማችን ከሃብት ክፍፍል፣ በዓለም ያሉት የፖለቲካ ፓርቲዎችና የፖለቲካ ልሂቃን ከሚከተሉት ርዕዮተ ዓለም እና አስተሳሰብ እንዲሁም መንግሥታት ከሚመሩበት የፖለቲካ ኢኮኖሚ ቅኝትና አተያይ አኳያ አንፃር ብቻ ሳይሆን፣ ከዘር ግንድና ከቋንቋ፣ ሃይማኖትና እምነት ወዘተ አኳያ ሲታይም አንድ ዓይነት/ Identical / ሳይሆን የብዙህነት(Pluralism) መናኸሪያ መሆኗን የዘርፉ ተመራማሪዎች በተጨባጭ ማስረጃዎች አስደግፈው ይገልፁታል፡፡ ይኸውም አሁን በዓለማችን በአሃዳዊ ሥርዓት (Unitary system) እንዲሁም በህብረ-ብሄራዊ ፌዴራሊዝም ስርዓት(multinational federalism) የሚመሩ፣ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የዘር ሐረጋቸው 86 ከሚሆኑ የተለያዩ ነገዶች እንደተገኘ ጥናቶች ያመለክታሉ፡፡  በዓለማችን ያሉት ብሄሮች፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ከምልክት ቋንቋ ውጭ መነሻቸው ዘጠኝ/9/ ዋነኛ “የቋንቋ ቤተሰብ” ማለትም  Indo-European, Sino-Tibetan, Niger-Congo, Afro-asiatic, Austronesia, Dravidian, Altaic, Austroasiatic and Tai-kadia languages በመባል ከሚጠሩ የፈለቁ 6,000 የተለያዩ ቋንቋዎች እንደሚናገሩ የቋንቋ ምሁራን ጥናቶችን አስደግፈው ይገልፃሉ፡፡ በኢትዮጵያ እየተነገሩ ያሉት የሚበዙት ቋንቋዎችም Afro-Asiatic  ከሚባል የቋንቋ ቤተሰብ እንደተገኙ የዘርፉ ምሁራን ያስረዳሉ፡፡

ዓለማችን ቋንቋ ብቻ ሳይሆን የሀይማኖትና የእምነት ብዙህነትም ሌላው መገለጫዋ ነው፡፡ ይኸውም እ.አ.አ. 2013 ተዘጋጅቶ በ(Wikipedia, free encyclopedia) የተሰራጨ አንድ ጥናት ከ2.2 ቢልዮን እስከ 6 ሚሊዮን ተከታዮች ያሉዋቸው 20 ትላልቅ ሃይማኖቶችና እምነቶች እንዳሉ አመልክቷል፡፡ እነዚህም  “Christianity, Islam, none religious/Atheist, Hinduism, Chinese traditional religion (Confucianism, Buddhism & Taoism) Buddhism, Ethnic religions, African traditional religions, Sikhism, Spiritism, Judaism, Baha’i, Jainism, Shinto, Cao Dai, Zoroastrianism, Tenrikyo, Ne0-paganism, Unitarian Universalism, & Rastafarianism” የሚባሉ ናቸው፡፡ ኢትዮጵያም በዋናነት ክርስትና/ኦርቶዶክስ፣ ካቶሊክና ፕሮቴስታንት/ እስልምና እንዲሁም ዋቄ ፈታን ጨምሮ የተለያየ እምነት የሚከተሉ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች በመቻቻልና በመከባበር በፍቅር የሚኖሩባት አገር ነች፡፡

ምድራችን ከፖለቲካል ኢኮኖሚ አስተሳሰብና ፌዴራሊዝም አወቃቀር አኳያም የተለያየ አስተሳሰብ የሚያራምዱ ኃይሎች የምትመራ ነች፡፡ በተለይም እ.አ.አ ከ1980ናዎቹ መጨረሻዎች አካባቢ ጀምሮ በዓለም የአስተሳሰብ የበላይነት ያገኘው የኒዮ-ሊበራሊዝም ዋነኛ አቀንቃኝ የነበሩት የቀድሞ የእንግሊዝ ጠ/ሚ/ር ሚስስ ማርጋሬት ታቸር በአንድ ወቅት “ህብረተሰብ ብሎ ነገር የለም”  “There is no such thing as society” ማለትም የፖለቲካል ኢኮኖሚ ሥርዓቱ በግለሰቦች ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ይህም የኒዮ-ሊበራል አስተሳሰብ አቀንቃኞች የግለሰቦች መብት ከተከበረ የብሄርና ብሄረሰቦች መብትም ይከበራል በሚል እምነት በግለሰብና በቡድን መብቶች መካከል ያለውን መስተጋብር በፍፁም እንደማይቀበል በገሃድ የሚያሳይ ነው፡፡ የኒዮ ሊበራል አተያይ ሁሉም የሰው ልጆች አንድ ናቸው፡፡ በጂኦግራፊ፣ በባህል፣ በቋንቋና በእምነት ቢለያዩም ፍላጐታቸው አንድ ዓይነት ነው የሚል አሃዳዊ ንድፈ ሃሣብ (monist theory)የሚከተል ነው፡፡

በአንፃሩ የተለያዩ ዋልታዎች (multi polar) የሚስተናገድባት ምድራችን፣ በየትኛውም የዓለም አቅጣጫ ያሉ ህዝቦች የሰው ልጆች በመሆናቸው ብቻ የሚጋሩዋቸው የጋራ እሴቶች (Universal values) እንዳሉ አሌ አይባልም፡፡ ሆኖም በተለያየ ባህል፣ ቋንቋ፣ እምነት፣ ስነ-ልቦና፣ የፖለቲካ የአመራር ዘይቤ እንዲሁም፣ ማህበረ-ኢኮኖሚ ሁኔታ ውስጥ የሚኖሩ በመሆናቸው ህብረ ብሄራዊ ዴዴራሊዝም (multinational federalism) ተከትለው የጋራ መግባባት ፈጥረው በመፈቃቀድና በመቻቻል ዴሞክራሲያዊ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት መስርተው፣ ከድህነት የተላቀቀና የበለፀገ ማህበረሰብ መስርተው ሊኖሩ ይችላሉ የሚል በብዙህነት ላይ የተመሰረተ የፌዴራል ሥርዓት አደረጃጀት ንድፈ ሃሣብ  (multi cultural theory)  የሚከተል ነው፡፡
በአጭሩ ከላይ የተገለፁ ጉዳዮች የሚያመለክቱት ዓለምም እንደ ኢትዮጵያ የብዙህነት መናኸሪያ መሆኗን ነው፡፡ ታዲያ ኢትዮጵያ ባለፉት 25 ዓመታት ብዙህነት ላይ የተመሠረተ ህብረ ብሄራዊ ፌዴራል ሥርዓት ለመመሥረት መታተሯ፣ ለምንድነው በአንዳንድ የፖለቲካ ልሂቃን (Political elites’) አተያይ ይህ ሥርዓት በቀጣይ ሃገሪቷን ይበታትናል፣ አንድነትን ያላላል? ህዝቦች ያናቁራል?  ወዘተ የሚባለው?  በመሬት ያለው እውነታስ እንደሚባለው ነው ወይ?  ኢትዮጵያ ባለፈው ሩብ ክፍለ ዘመን ህብረ-ብሄራዊ ፌዴራሊዝም በመከተሏ ተጠቀመች ወይስ ተጐዳች በሚሉት ጉዳዮች አንድ ሁለት ማለቱ አይከፋም፡፡
እንደሚታወቀው ኢትዮጵያ አገራችን የሰው ልጆች መገኛና ረዥም ዘመን ታሪክ ያላት አገር ናት፡፡ ይህንን ረዥም ታሪክ በዚህ ፅሑፍ መዳሰስ የሚሞከር አይደለም፡፡ ሆኖም በአጭሩ የአገራችን ታሪክ በርካታ ሺህ ዓመታት ያስቆጠረ ብቻ ሳይሆን ልዩ ልዩ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የየራሳቸው አሻራ ያሳረፉበት የረዥም ታሪክ ሂደት ነወ፡፡ ለዚህም ነው በአንድ ወቅት ታላቁ መሪ ታጋይ መለስ ዜናዊ “አባይ ወንዝን አባይ ለማሰኘት ከየአቅጣጫው የሚፈሱ የተለያዩ ወንዞች ተቀላቅለው እንደሚፈጥሩት ሁሉ፣ የኢትዮጵያ ታሪክ በርካታ ትንንሽ ጅረቶች እየተቀላቀሉት በትልቁ እንደሚፈስ ወንዝ መታየት ያለበት ነው” በማለት የገለፀው፡፡ የኢትዮጵያ የታሪክ ሂደት ወታደራዊ የፋሽስታዊ ደርግ አገዛዝ እስከወደቀ ድረስ በነበሩት ከሦስት እስከ አራት ሺህ ዓመታት ድረስ ጠቅለል ብሎ ይቀመጥ ቢባል፣ አራት ዓበይት ጉዳዮች የተከሰተበት ሂደት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ይኸውም 1ኛ/ ኢትዮጵያ አገራዊ ነፃነታቸውን አስከብረው የኖሩ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች አገር መሆኗ 2ኛ/ ብዙህነት በአግባቡ ማስተናገድ ተስኗት የቆየች የብዙህነት አገር፣ 3ኛ/ ከገናና ሥልጣኔ ወደ አስፈሪ ተመፅዋችነት ለመሸጋገር የተገደደች እንዲሁም  4ኛ/ የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ለእኩልነታቸው ታግለው የሥልጣን ባለቤትነታቸውን ያረጋገጡባት እና ከ25 ዓመታት በፊት ከዕንቅልፍ ተነስታ በዕድገት ጐዳና እየገሰገሰች ያለች አገር መሆኗ የሚሉት ሊገለፁ ይችላሉ፡፡   

የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የግልና የቡድን መብቶችን ለዘመናት አፍኖ ለከፉ ድህነት፣ ኋላቀርነት፣ ሞት፣ ስደትና እንግልት የዳረጉዋቸው የመሳፍንትና የአምባገነኑ ወታደራዊ የፋሽስት ደርግ አገዛዝ፣ በኢህአዴግ መሪነት በኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች መራራ የህይወትና የንብረት መስዋዕትነት ግብአተ መሬታቸው የተፈፀመበት 25ኛ የብር ኢዮቤልዩ በዓል ለማክበር ዋዜማ ላይ ባለንበት በአሁኑ ወቅት ሂደቱን ወደኋላ መለስ ብለን ብንቃኘው፣ በበርካታ ድሎች ታጅበን ማለትም በሁሉም ዘርፍ በተመዘገቡ ድሎች እያንዳንዱ ዜጋ በየደረጃው ተጠቃሚ መሆን መቻሉንና መጀመሩን በገሃድ የምናይበት ነው፡፡
ከፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓት ግንባታ አኳያ ሲታይ አገራችን ረዥም ርቀት ተጉዛለች፡፡ ይኸውም በጠመንጃ አፈሙዝ እና “አንድ ህዝብ” በሚል የአስተዳደር ዘይቤ (Assimilation)፣ ማንነታቸው ተረግጦና ብዙህነታቸው እንዲደፈቅ ተደርጐ ለዘመናት የቆዩ የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ማንነታቸው ተከብሮ በእኩልነት፣ በመፈቃቀድና በመከባበር በመኖር ላይ ናቸው፡፡ በመሆኑም እስከ አሁን ባለው ሂደት በኢፌዴሪ የፌዴሬሽን ም/ቤት ዕውቅና ያገኙ ከ75 በላይ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች  የራሳቸውን አካባቢ ራሳቸው በራሳቸው በማስተዳደር ላይ ናቸው፡፡ የሃይማኖት፣ የፆታ እኩልነት በተግባር ተረጋግጧል፡፡ ከ80 በላይ የተለያዩ ቋንቋዎች እኩል ዕውቅና አግኝተው የየአካባቢው መስተዳደር የመግባቢያና የሥራ ቋንቋ ሆነው በማገልገል ላይ ናቸው፡፡ አማርኛም የፌዴራል መንግሥት የሥራ ቋንቋ ሆኖ በማገልገል ላይ ነው፡፡ የተለያዩ ርዕዮተ ዓለማዊ አስተሳሰብ ያላቸው 75 በላይ ፓርቲዎች በሃገሪቱ በሕጋዊ መንገድ በመንቀሳቀስ ላይ ናቸው፡፡ የተለያዩ አመለካከት የሚያንፀባርቁ፣ የኤሌክትሮኒክስ፣ የህትመትና ዘመናዊ/ማህበራዊ ሚዲያ አውታሮችም ተስፋፍተዋል፡፡

ኢትዮጵያ ባለፉት 25 ዓመታት ማንነትን መሠረት ያደረገ ህብረ-ብሄራዊ ፌዴራሊዝም ሥርዓት አተያይ መከተሏ፣ በህዝቦች ዘንድ በመተማመን፣ በመፈቃቀድ ላይ የተመሠረተ ዴሞክራሲያዊ አንድነት ይበልጥ ስር እየሰደደ እንዲሄድ አድርጐታል፡፡ ኢትዮጵያ እየተከተለችው ያለው የፌዴራል ሥርዓት በሚበዙት ኢትዮጵያውያን ዘንድ ብቻ ሳይሆን በዓለም አቀፍ ደረጃም ተቀባይነት እንዳለው የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የትምህርት፣ የሳይንስና ባህል ድርጅት(UNESCO) እንዲህ ብሏል፡፡   "Culture takes diverse forms across time and space. This diversity is embodied in the uniqueness and plurality of the identities of the groups and societies making up humankind. As a source of exchange, innovation and creativity, cultural diversity is as necessary for humankind as biodiversity is for our nature." (UNESCO Paris, 2004)
አዎን!  ህብረ- ብሄራዊነታችን ለእኛ ለኢትዮጵያውያን ዕዳ ሳይሆን ውበታችንና ፀጋችን ነው፡፡ ይህ ለዘመናት የቆየ ብዙህነት ወደ አደባባይ መውጣቱ፣ ባለፉት 25 ዓመታት ማንነት በይፋ ዕውቅና ማግኘቱ ይበልጥ ኢትዮጵያዊነትን አጠናከረ እንጂ፣ አንድም ብሄር ወይም ብሄረሰብ ከኢትዮጵያ ልገንጠል አላለም፡፡ በእርግጥ አልፎ አልፎ እዚህ እዛም ግጭቶች መከሰታቸው የሚካድ አይደለም፡፡ ሆኖም በየወቅቱ የተከሰቱ ችግሮች ህብረ-ብሄራዊ የፌዴራል ሥርዓቱ አወቃቀሩ የወለዳቸው አይደሉም፡፡ ሊሆኑም አይችሉም፡፡ በዋነኛነት ችግሮቹ የተፈጠሩት የኪራይ ሰብሳቢነት የፖለቲካል አ.ኮኖሚ የበላይነት ስለያዘ ነው፡፡ ለዚህ ነበር ታላቁ መሪ ታጋይ መለስ ዜናዊ በአንድ ወቅት “የድህነት ዘበኛ የነበረው ደርግ አሁንም አለ” ያለው፡፡ ይህ ማለት የኪራይ ሰብሳቢነት መገለጪያ የሆኑት ትምክህት፣ ጠባብነት፣ አክራሪነትና አሸባሪነት ተቸንፈው ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ የበላይነት አግኝቶ፣ በምክንያት የሚደግፍና የሚቃወም አስተሳሰብና እሴት(Rational thinking) እስከሚገነባ ድረስ ነገም ከነገ ወዲያም አልፎ አልፎ ግጭት መከሰቱ አይቀሬ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የኢፌዴሪ መንግሥትና የኢትዮጵያ ህዝቦች ማድረግ የሚችሉት ነገር ቢኖር፣ በተለያዩ ምክንያቶች በየአካባቢው የሚነሱ ግጭቶች ፀረ-ሰላምና ፀረ-ህዝብ ኃይሎች ለአፍራሽ ዓላማቸው መጠቀሚያ እንዳያደርጉዋቸው መመከትና መከላከል ነው፡፡
የህብረ-ብሄራዊ ፌዴራሊዝም አወቃቀርን የማይደግፉ ኃይሎች ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች በተለያዩ የአፍ መፍቻ ቋንቋ መጠቀማቸው፣ ኢትዮጵያን እንደሚበታትናትም ሲሰብኩ ከርመዋል፡፡ሆኖም ኢትዮጵያ የምትከተለው አካሄድ ተገቢነት እንዳለው የተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ ሳይንስና የባህል ድርጅት(UNESCO)  እንደሚከተለው ያስቀምጠዋል፡፡
 "Local content is the expression of a community's knowledge and experience, and the process of creating and disseminating provides opportunities to the members of the community to interact and communicate with each other, expressing their own ideas, knowledge and culture in their language." (UNESCO Paris, 2004)

አገራችን 25ኛውን ዓመት የግንቦት 20 የብር ኢዮቤልዩ በዓል የምታከብረው በራሷ የዘመን አቆጣጠር 2017 የምትደርስበትን ዝቅተኛ መካከለኛ ገቢ (Lower middle income) ራዕይ ለማሳካት፣ እና የተያያዘችውን የዕድገት ግስጋሴ ለማስቀጠል ወሳኝ የሆነው የቀጣይ አምስት ዓመታት /ከ2008-2012 ዓ.ም./ 2ኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ  መተግበር በጀመረችበች በመሆኑ ልዩ ያደርገዋል፡፡
ባለፉት 25 ዓመታት በኢህአዴግ እየተመራች፣ የራሷን ውስጣዊ ሁኔታ መሠረት አድርጋ የቀመረችው የነፃ ገበያ ኢኮኖሚ፣ ሊበታትናት አፋፍ ላይ አድርሷት የነበረውን ፋሽስታዊ ወታደራዊ አገዛዝ መገርሰስ ብቻ ሳይሆን፣ ህዝቦችዋን እግር ተወርች አስሮ ተመፅዋች ያደረጋቸውን ድህነትም በመደርመስ ላይ ነች፡፡ ይኸውም በ1988 ዓ.ም. ከድህነት ወለል በታች (Under absolute poverty) ይማቅቅ የነበረው 45.5 ከመቶ ህዝብ፣ በ2007 ዓ.ም.  ወደ 22 ከመቶ ዝቅ እንዲል አድርጋለች፡፡ ይህ በራሱ በጣም ትልቅ ድልና ዕድገት ነው፡፡ የነብስ ወከፍ ገቢም በ2003 ዓ.ም. 396 የአሜሪካ ዶላር የነበረው በ2007 ዓ.ም. 691 የአሜሪካ ዶላር ደርሷል፡፡ በማህበራዊ ዘርፍም ኢትዮጵያ የሚሊኒየም ግቦች ካሳኩ አገሮች አንዷ ሆናለች፡፡ የገቢ ክፍፍሉም “Gini coeffiencient” በሚባለው መለኪያ 0.3 በመሆኑ ፍትሃዊ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት የቱሪስትና የውጭ ኢንቬስተሮች መዳረሻ ሆናለች፡፡ ለአብነት ያህል 1984 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ሦስት/3/ የውጭ ባለሃብቶች ብቻ ነበሩ፡፡ በአሁኑ ጊዜ ግን በየዓመቱ በአማካይ በተለያዩ መስኮች የሚሰማሩ ከ500-600 የውጭ ባለሃብቶች ወደ አገራችን ገብተው በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛሉ፡፡ ከ2003 -2007 ዓ.ም. ባለው የመጀመሪያው የዕድገትና የትራንስፎርሜሽን ዕቅድም በየዓመቱ በአማካይ ብር 10 ቢሊዮን የውጭ ቀጥታ ኢንቨስትሜንት(Foreign direct Investment) በመሳብ ወደ ተግባር ማሸጋገር ተችሏል፡፡ ባለፉት ዓመታት ብር 7.48 ቢልዮን ካፒታል ያላቸው 132 ፕሮጀክቶች ወደ ምርትና አገልግሎት ተሸጋግረዋል፡፡ እነዚህ ፕሮጀክቶች በ10 ሺዎች ለሚቆጠሩ ዜጐች ቋሚና ጊዜያዊ የሥራ ዕድሎች ፈጥረዋል፡፡
ይህ ሁሉ ውጤት በዋነኛነት በታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ ሃሳብ አፍላቂነትና መሪነት የተቀመረው የኢትዮጵያ ብሄር ብሄረሰቦችና ህዝቦች “የጋራ ፕሮጀክት” የሆነው የህዳሴው መስመር ነው፡፡ በአጭሩ የውጤቱ ባለቤቶች የሆኑት የኢፌዴሪ መንግሥት እና የኢትዮጵያ ህዝቦች እጅ ለእጅ ተያይዘው ቀንና ሌሊት በመረባረባቸው ድህነት ወገቡ እየተቆረጠ ኢትዮጵያ ወደ ከፍታ ማማ እየተጓዘች ነው ያለችው፡፡

ከኢፌዴሪ ሕገ-መንግሥት የፈለቀው የህዳሴው መስመር ካስገኛቸው ውጤቶች በዋነኛነት የሚጠቀሰው ህብረ-ብሄራዊ የፌዴራሊዝም ዴሞክራሲያዊ የመድብለ ፓርቲ ሥርዓታችን የኢትዮጵያ መሠረት መሆኑ፤ በአራቱም አቅጣጫ ያሉት የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች የጋራ መግባባት ላይ መድረሳቸው ነው፡፡ ይህ የአስተሳሰብ ለውጥ ዋነኛ ጠላታቸው የሆነውን ድህነት በዕውቀታቸው፣ በጉልበታቸውና ገንዘባቸውን አቀናጅተው እንዲፋለሙ አድርጓቸዋል፡፡ በተለይ ወጣቱ ትውልድ የነገ ብሩህ ተስፋ በቅርብ ርቀት አሻግሮ እያየ ራሱ ጥሮና ግሮ መለወጥ እንዳለበት በአስተሳሰብ ብቻ ሳይሆን በተግባርም በጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ተደራጅቶ እያደረገው ያለው ጥረት ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡

አያቶቻችንና ቅድመ አያቶቻችን ከ120 ዓመት በፊት አድዋ ላይ የጣልያን ቅኝ ገዢዎችን፣ እንዲሁም ከ75 ዓመታት በፊት ደግሞ የፋሽስት ጣልያን ድል አድርገው ነፃነታቸውን እንዳስከበሩ ሁሉ፤ የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች ባለፉት 25 ዓመታት ካደረጉዋቸው ወሳኝ ጉዳዮች አንዱ “የይቻላል” መንፈስ ጨብጠው “የታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብን” በራሳቸው ዕውቀት፣ ጉልበትና ገንዘብ ገንብተው፣ ትላንት መርፌ መሥራት አትችሉም የተባሉበት አንገት የሚያስደፋ አስተሳሰብ ሰብረው፣ የሚያስብ ጭንቅላትና የሚሠሩ እጆች ያሉዋቸው መሆናቸው እና ከተመፅዋችነት ወጥተው በራሳቸው ዓቅም የኢኮኖሚ ነፃነታቸውን በማረጋገጥ ላይ መሆናቸው በተጨባጭ ለዓለም ማሕብረሰብ አሳይተዋል፡፡ ባለፉት ዓመታት ከተመዘገቡት ድሎችም ከሁሉም የላቀው የኢትዮጵያ ብሄር፣ ብሄረሰቦችና ህዝቦች መሠረታዊ የአስተሳሰብ ለውጥ ማስመዝገባቸው ነው ቢባል እውነታውን መግለፅ ነው፡፡
የኢትዮጵያ የህዳሴ ግድብ 5ኛው ዓመት በዓለም “ታላቁ የህዳሴ ግባችን የማንነታችን አሻራ ያረፈበት የህዳሴአችን ብርሃን ነው” በሚል መሪ ቃል የታላቁ መሪያችን ታጋይ መለስ አደራ ጠብቀው ያጋመሱትን የህዳሴው ግድብ ግንባታ በተባበረ ክንድ ለማጠናቀቅ በተለያየ መልክ በመረባረብ ላይ ናቸው፡፡ ይህም ታላቁ የኢትዮጵያ ህዳሴ ግድብ ብዝሃነትን ባከበረና ዴሞክራሲያዊ አንድነታችን ባጠናከረ አገባብ የምንፈጥራት የበለፀገች ኢትዮጵያ ማሳያ ነው፡፡ በአጭሩ ይህ ዓለምን ያስደመመ በጐ ተግባር ለብዙህነታችን ዕውቅና መስጠታችንና ህብረ ብሄራዊ ፌዴራሊዝም መከተላችን ትክክል ብቻ ሳይሆን በተባበረ ክንዳችን ምን ያህል ተአምር መሥራት እንደምንችል በጉልህ የሚያሳይ ነው፡፡

በቀጣዩ ወር የምናከብረው 75ኛው የአልማዝ ኢዮቤልዩ የነፃነት በዓላችንም ድህነትን እየደረመስን የቅድመ አያቶቻችን፣ የአያቶቻችን ታሪክ የምንደግመው ብዝሃነታችን ላይ በገነባነው አንድነታችን ላይ በመሆኑ ድሉ ድርብ ያደርገዋል፡፡
በአጭሩ ዓለምም ኢትዮጵያም የብዝህነት መናኸሪያ ናቸው፡፡ በመሆኑም ከሁለት ወራት በኋላ በድምቀት የምናከብረው የግንቦት 20 የብር ኢዮቤልዩ 25ኛው ዓመትም ኢትዮጵያ ብዝህነት ፀጋ መሆኑን በውል ተገንዝባ በየትውልዱ የአንፀባራቂ ድል ሀገር መሆኗን ለዓለም በማሳየት ነው፡፡

No comments:

Post a Comment