EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Friday, 26 June 2015

አዳዲሶቹ ስምምነቶች

በሠይፈ ደርቤ
አምስተኛው አገር አቀፍ ምርጫ በአገራችን እስካሁን ከተካሄዱ ምርጫዎች በመራጩ ህዝብና በተፎካካሪዎች ተሳትፎም ሆነ በዴሞክራሲያዊነቱ የተሻለ ነው። 36 ነጥብ 8 ሚሊየን ህዝብ የመራጭነት ካርድ በወሰደበት በዚህ ምርጫ ከ33 ሚሊየን በላይ መራጭ ድምፅ ሰጥቷል። 58 ያክል ፓርቲዎችም ተፎካክረውበታል። ይህም ህዝቡ የሚያስተዳድረውን መንግስት የመሾምና የመሻር ህገ መንግስታዊ መብቱን ዋጋ ይበልጥ የተገነዘበበትና ተቃዋሚ ፓርቲዎችም የመንግስት ስልጣን የሚያዘው ከምርጫ ኮሮጆ በሚገኝ ድምፅ ብቻ መሆኑን ተገንዝበው ወደ መድረኩ የወጡበት አጋጣሚ ሆኖ አልፏል።
ምርጫው በቁጥራቸው በርካታ ነገር ግን በያዙት የፖለቲካ ፍልስፍና በሁለት ጎራ የተሰለፉ የፖለቲካ ፓርቲዎች በነፃ፣ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ በአስተሳሰብ ተፋልመው የልማታዊ ዴሞክራሲ አስተሳሰብ ገንኖ የወጣበት፣ የአስተሳሰቡና የተግባሩ ባለቤት የሆነው ፖለቲካ ፓርቲም በህዝቡ ሙሉ ፍቃድ የተጀመረውን አገራዊ እድገት ለማስቀጠል ይሁንታ ያገኘበት ነው።
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ እንዳስታወቀው ከ547 የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመቀመጫ ወንበሮች 546ቱን ኢህአዴግና አጋሮቹ አሸንፈዋል። ኢህአዴግ በተናጠል ካገኛቸው 500 ወንበሮች ውስጥ 212ቱ በሴቶች የተያዙ መሆናቸው ደግሞ የሴቶች ፖለቲካዊ ተሳትፎ እያደገ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡
መራጩ ህዝብ ለኢሕአዴግና አጋሮቹ ሙሉ መቀመጫ ሲሰጥ የኢህአዴግን የእስካሁን አፈፃፀምና የቀጣይ ራዕይ ግምት ውስጥ አስገብቷል። ለተቃዋሚው ጎራ ድምፁን ሲነፍግ ደግሞ ተቃዋሚው ሀይል በአስተሳሰብ ቀድሞ መሸነፉን በሚያሳብቅ መልኩ በራሱ አንደበት አማራጭ እንደሌለው ማረጋገጡን ተረድቷል። ይህ ማለት ተመራጩ መንግስት በስልጣን ዘመኑ ያከናወናቸው ዘርፈ ብዙ የልማት ስራዎችና የህዝቡን ተጠቃሚነት ያረጋገጠባቸው ስኬቶች ለ5ኛ ጊዜ በህዝብ ለመመረጡ መተኪያ የሌላቸው ምክንያቶች ሲሆኑት “የማያጠግብ እንጀራ ከምጣዱ ያስታውቃል” እንዲሉ አማራጫችው ኢህአዴግን መቃወም ብቻ መሆኑን በንግግራቸውና በተግባራቸው ያሳዩ ፖለቲከኞችን ህዝቡ በጊዜ ጥግ አስይዟል።
በምርጫ 2007 ዴሞክራሲያዊ ስርዓቱ ባስገኘው ህገ መንግስታዊ የመደራጀት መብት ትላንት ተፈጥረው ለራሳቸው ብኩርና የሰጡ አንዳንድ ተቃዋሚዎች ምርጫውን ለሰላማዊ ውድድር ሳይሆን ለብጥብጥ አጋጣሚ ለመጠቀም ብርቱ ጥረት አድርገዋል። በአሸባሪው አይ ኤስ የተገደሉ ዜጎቻችንን ለማሰብና የሽብር ቡድኑን ለማውገዝ የተጠራውን ሰልፍ ሳይቀር ለጥፋት ተልዕኳቸው ማስፈፀሚያ ለመጠቀም የሞከሩ ተቃዋሚዎች አወዳደቃቸው የከፋ ሆኗል። ህዝቡ  በዚህ ምርጫ ሽብርና የጦርነት ስጋት በበዛበት አህጉር የሰላም ደሴትነቷን ያረጋገጠችውን አገሩን ነባራዊ ሁኔታ ለማስቀጠል አቋም በመያዝ ለሰፈነው ሰላም ውግንናውን ሲያሳይ በአንፃሩ ነውጥ ናፋቂዎቹ የብጥብጥ ቀዳዳ እንዳያገኙ ድምፁን ነፍጓል።
አጠቃላይ ድምፅ ከሰጠው ህዝብ መካከል ከ82 በመቶ በላዩ ለኢሕአዴግ ድጋፉን ሲገልፅ ታዲያ ከፓርቲው ጋር አዳዲስ ስምምነቶችን ለመዋዋል ነው፡፡ አዲሱ ስምምነት 5ኛው አገር አቀፍ ምርጫ የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ልዕልናን በማረጋገጥና የሙሉ መቀመጫ ባለቤት በማድረግ ለመንግስትነት ስልጣን ያበቁት ዜጎች ታዲያ ኢሕአዴግ እንዲፈፅምላቸው የሚጠብቁት አለ።
በዚህ ስምምነት በኢህአዴግ ላይ ታላቅ ኃላፊነት በመጣል ለሁለተኛው የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ እንዲተጋ የመንግስትነት አደራ ሰጥተዋል። እግረ መንገዳቸውንም ለምዕራባውያን ገናና የሆነው የኒዮ ሊበራል አተያይ በኢትዮጵያ ሊሞከር እንደማይችል ይልቁንም ከድህነትና ኋላቀርነት የሚያላቅቃቸው የልማታዊ ዴሞክራሲ መስመር መሆኑን አረጋግጠዋል። በመሆኑም በአዲሱ ስምምነት መሰረት ተመራጩ የፖለቲካ ፓርቲ ይህንን ከሞላ ጎደል ሙሉ ተቀባይነት ያገኘውን ልማታዊ ዴሞክራሲያዊ አስተሳሰብ በብቃት የሚመሩ፣ ከምንም በላይ ደግሞ የህዝብን አደራ ያስቀደሙ አመራሮችንና አባሎቹን ከፊት በማሰለፍ ወገብ በሚያጎብጠው ተደማሪ የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የህዝቦችን ተጠቃሚነት ይበልጥ ለማረጋገጥ በእልህ እንዲሰራ ሃላፊነት ተሰጥቶታል።
ገዢው ፓርቲ በእስካሁኑ ጉዞ በልማት፣ በመልካም አስተዳደር፣ በሰላም ማስከበርና በሌሎች የዴሞክራሲ ማስፈን ተግባራት ከከፍተኛ እስከ ታችኛው አመራር ድረስ ቀን ተሌት የሚሰሩ አመራሮችና ሙያተኞች እንዳሉት ሁሉ በሌሎች ድካምና ጥረት ተሸጉጠው የግል ፍላጎታቸውን ለማሳካት የሚተጉ ጥቂቶች እንዳሉ በፅኑ በመገንዘብ ከምንም በላይ በህዝባዊ ወገንተኝነት ጉዳይ የማይደራደር መሆኑን ማሳየትም የስምምነቱ አካል ነው።
በመሆኑም ተመራጩ ፓርቲ ሙሉ መቀመጫ ያገኘሁት የዝረራ ያህል ነው ብሎ ሳይኩራራ ይልቁንም በአብላጫ ድምፅ ቆጠራ ያሸነፈ መሆኑንና ጥቂትም ቢሆን ድምፅ ያልሰጠው እንዳለ በመረዳት ካለፈውም በላይ ለመስራት ከወዲሁ መዘጋጀት ይኖርበታል። ከሁለተኛው ዘመን የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ የቤት ስራዎች ጋር በሚጣጣም ጉልበት፣ እውቀት፣ ታማኝነት፣ ፍላጎትና ልምድ ባላቸው አመራሮች እቅዶቹን ለመፈፀም ራሱን ፈትሾ ወደ ተግባር መግባት ይጠበቅበታል። የመረጠውም፣ ያልመረጠውም ህዝብ ፍላጎት ምን እንደሆነ መለየትም አለበት።
አገራችን እየተገበረችው ባለው የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ውስጥ በህጋዊና ሰላማዊ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚዎች እየተደመጡ፣ አሸናፊው ፓርቲም ህዝቡ የሰጠውን ታላቅ አደራና ኃላፊነት እየተወጣ እንዲሄድ በጋራ አገራዊ ጉዳዮቻችን አንድ ሆነን መዝለቅ ይጠበቅብናል። በመሆኑም በህዝብ ድምጽ የተሸነፈው ተቃዋሚም ያልመረጠውን አብላጫ ህዝብ አክብሮ ካሸነፈው ፓርቲ ጋር በጋራ አገራዊ ጉዳዮች ተባብሮ ሊሰራ ይገባል።
ክብር ለመራጩ ህዝብ!!

No comments:

Post a Comment