EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Wednesday 11 February 2015

ከህዝብ ያልወገነ የተቃውሞ ፖለቲካ

ሰሞኑን በፌስቡክ ገፃችን ባወጣንው አንድ ጽሁፍ በፖለቲካው መስክ የሚደረገውን ትግል አለም አቀፋዊ ገፅታ ከቃኘን በኋላ በሀገራችን ያለው ነባራዊ ገፅታ ምን እንደሚመስልና ምን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የእናንተን እይታ ጠይቀናችሁ ነበር፡፡ ፅሁፉን መሰረት አድርጋችሁ አስተያየት ለሰጣችሁን በሙሉ ምስጋናችን ይድረሳችሁ እንላለን፡፡ በዚህኛው ፅሁፍ ደግሞ የሀገራችን የተቃውሞ ፖለቲካ እንቅስቃሴ ምን እንደሚመስል ከፓርቲዎቹ አጠቃላይ ሁኔታ በመነሳት እንቃኛለን፡፡
ዜጎች ተደራጅተው የሚፈፅሙት የፖለቲካ ትግል ከምንም በፊት ዴሞክራሲያዊ መሆን አለበት፡፡ በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ሆነው የሚያደርጉት ትግል ለሚወክሉት የህብረተሰብ ክፍል ጥቅምና ፍላጎት ቅድሚያ የሚሰጥ፤ ለዚህም ሲባል የራስን ጥቅም አሳልፎ መስጠት ካስፈለገ እሱንም እስከመፈፀም የሚደርስ ነው፡፡ አንድ አስተያየት ሰጪ እንደጠቀሰው ለማህበረሰቡ ጎጂ ሆኖ ሳለ የግለሰቦችን ወይም የተወሰኑ ቡድኖችን ፍላጎት ለማርካት የሚደረግ ትግል ግን በመሰረቱ ፀረ ዴሞክራሲያዊ ነው፡፡


የህዝብን ጥቅምና ፍላጎት መሰረት አድርጎ የሚፈፀም ትግል ባለፈው ፅሁፋችን ለማብራራት እንደሞከርነው ሰላማዊ የፖለቲካ ከባቢን በመፍጠር፤ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት እንዲጠናከሩ በማድረግ፤ ዜጎች በምክንያት የመደገፍና የመቃወም ባህልን እንዲያዳብሩ በማድረግ፤ ለፓርቲዎች ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ምቹ ሁኔታን በመፍጠር፤ በውድድር ነጥረው የወጡ የፖሊሲ አማራጮችን በማቅረብ፤ ወዘተ… ለዴሞክራሲያዊ ስርዓቱ ቀጣይነት ዋስትና ይሰጣል፡፡
ይህ በፅንሰ ሃሳብ ደረጃ ተቀባይነት ያለው ጉዳይ በሀገራችን እንዴት እየተፈፀመ እንዳለ ለማየት የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎችን ሁኔታ ማጤን ይገባል፡፡ በሀገራችን ያሉት ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለይ ደግሞ ፅንፈኛ አቋም ይዘው የጥላቻ ፖለቲካ የሚያራምዱት ሃይሎች ያሉባቸው መሰረታዊ ችግሮች ፓርቲዎቹን በእነዚህ ትግል መመዘኛዎች ሲለኩ ከደረጃ በታች እንዲያርፉ ያደርጓቸዋል፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በብዙ ችግሮች የተተበተቡ ቢሆኑም ከዚህ ርዕሰ ጉዳይ ጋር የተያያዙትን ብቻ ለማንሳት እንሞክራለን፡፡
አማራጭ አስተሳሰብ የሌላቸው መሆን
የሀገራችንን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለከፍተኛ ትዝብት የዳረጋቸው ጉዳይ ቢኖር ይህ ነው የሚባል አማራጭ የፖለቲካ፤ ኢኮኖሚና ማህበራዊ መስመር የሌላቸው መሆናቸው ነው፡፡ የእድሜያቸውን ያህል ከሀገራዊና አለም አቀፋዊ ተለዋዋጭ ነባራዊ ሁኔታዎች ጋር አብሮ እያደገ የሚሄድ የርዕዩተ አለም አማራጭ ለህዝብ ለማቅረብ ተስኗቸው ይታያሉ፡፡ ይባስ ብለው አንዳንዶቹ የተለያየ ርዕዮተ አለም ይዘው ይጣመሩና የትኛውን መስመር አይቶ ህዝቡ ድምፁን እንዲሰጣቸው እንደሚፈልጉ ሲጠየቁ ስልጣን ከያዙ በኋላ እንደሚያቻችሉት ሲናገሩ ተደምጠዋል፡፡ እንደ መሬት፤ የብሄር ብሄረሰቦች እኩልነት መብት፤ የመንግስት ስርዓት ባሉ የሀገራችን ህዝቦች የዘመናት የፖለቲካ ጥያቄዎች ላይ ወጥ አቋም ሳይኖራቸው ኢሕአዴግን ስለተቃወሙ ብቻ አንድ ነን ይሉናል፡፡
ብዙዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ለስሙ የኒዮ ሊበራል ፍልስፍናን እንከተላለን ቢሉም በዚሁ መስመር ላይ እንኳን ከጥራዝ ነጠቅነት ያለፈ ግንዛቤው የላቸውም፡፡ ለዚህም ነው እንከተለዋለን ከሚሉት ፍልስፍና ጋር የሚጋጭ የመርህ ጥሰት ሲፈፅሙ የሚታዩት፡፡ ለአብነት በዚህ ፍልስፍና ላይ ተመርኩዘው የብሔር ጥያቄን የማይቀበሉ ወይም እውቅና የማይሰጡ ፓርቲዎች ብሔርን መሰረት አድርገው ከተደራጁ ፓርቲዎች ጋር ውህደት ይፈጥራሉ፡፡ በተመሳሳይ በአንድ በኩል ብሔር የሚባል ነገር የለም /የብሄር ጉዳይ የቡድን መብት ስለሆነ/ ሲሉ ይቆዩና መለስ ብለው ደግሞ የአንድን ብሔር ስም በማንሳት በደል እንደደረሰበት ሊሰብኩን ይሞክራሉ፡፡
የውስጠ ድርጅት ኢ ዴሞክራሲያዊነት
አንድ ፓርቲ በዴሞክራሲያዊ አካሄድ በህዝብ በተገኘ ይሁንታ ሀገር ለመምራት እችላለሁ ብሎ ከማሰቡ አስቀድሞ በራሱ ዴሞክራሲያዊ መሆኑን ማረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ በራሱ ዴሞክራሲያዊ ያልሆነ የፖለቲካ ተቋም ለሌሎች ዴሞክራሲን ማስፈን የሚያስችል አቅም ከየትም ሊያመጣ አይችልም፡፡ ቢሞክርም ሳያርሱ እንደመዝራት ነው የሚሆንበት፡፡
በሀገራችን የተቃዋሚ ፖለቲካ ድርጅቶች ለህዝብና ለሀገር አማራጭ የፖሊሲና የርዕዮት አለም ሃሳብን በማቅረብ በኩል ያልተሳካላቸው መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ ቢያንስ ጠንካራና ዴሞክራሲያዊ የሆነ የፓርቲ አደረጃጀትና አሰራር ፈጥረው ተግባራዊ ማድረግ እንኳን አልቻሉም፡፡
ፓርቲዎቹ ጠንካራ፣ ችግር ፈቺና ሊያሰራ የሚችል የፓርቲ መተዳደሪያ የውስጥ ደንብ ቀርፀው ተግባራዊ ማድረግ ባለመቻላቸው አመራርና አባሎቻቸው የፓርቲ ዲሲፕሊን ጥሰቶችን በስፋት ይፈፅማሉ፡፡ ከፓርቲ አመራሮች አሿሿም አንስቶ እስከ ገንዘብ አስተዳደር በርካታ ተግባራትን ከፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ ውጭ ይፈፅማሉ፡፡ በእነዚህ ጉዳዮች ላይ የልዩነት ሃሳብ ሲነሳ በመወያየት ከመፍታት ይልቅ እርስ በእርስ አሳፋሪ በሆነ መንገድ ሲወነጃጀሉና ሲዘላለፉ ማየት እየተለመደ ነው፡፡
የጥላቻ ፖለቲካ አራማጆች መሆናቸው
አብዛኛዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች በሀገራችን ተግባራዊ እየተደረገ ባለው የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ የድርሻቸውን ለመወጣት ቁርጠኝነት የሌላቸው መሆናቸው ሌላው ተጠቃሽ ድክመታቸው ነው፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች ገዢውን ፓርቲ ጨምሮ ከሌሎች ህግን አክብረው ከሚንቀሳቀሱ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጋር በጋራ ጉዳዮች ተቀራርቦ ከመስራት ይልቅ እንደ ጠላት በመፈረጅ ጥላቻና መለያየትን ያሰርፃሉ፡፡
በሰለጠነ መልኩ ከገዢው ፓርቲ ጋር ለመወያየት ፍላጎት ያሳዩ ፓርቲዎችን እንደከሃዲና የገዢው ፓርቲ አገልጋይ አድርገው በመሳል በህብረተሰቡ ዘንድ ተቀባይነት እንዳይኖራቸው ለማድረግ ዘመቻ ያካሄዱባቸዋል፡፡ እነዚህ ተቀራርቦ መስራትን ሳይሆን ጥላቻና መራራቅን የሚሰብኩ ፓርቲዎች ሌላው ቀርቶ እርስ በእርሳቸው እንኳን ‹‹ከእኔ በላይ ፓርቲ የለም›› በሚል ፉከራቸው የሚናናቁ ናቸው፡፡ አንድኛው አስተያየት ሰጭ የእኛ ሀገር ታቀዋሚዎች መቃዋም ማለት የሀገርን ጥቅም በጅምላ መቃወም ይመስላቸዋል ያለው ከዚህ በመነሳት ይመስላል፡፡
ለህዝብ ጥቅም ያልወገነ ተቃውሞ
የሀገራችን ፅንፈኛ ተቃዋሚ ፓርቲዎች አነሳስ በሚያቀርቡት የፖለቲካ አማራጭ ተወዳድረው ህዝብ እንዲመርጣቸው ሳይሆን ገንዘብ እየላከ የሚፈልገውን ጉዳይ እንዲፈፅሙለት ተልዕኮ የሚሰጣቸውን አካል ማገልገልን መሰረት ያደረገ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ የትግል አቅጣጫቸውና ትግበራው የሚመራው በመርህና ወጥነት ባለው መንገድ ሳይሆን የገንዘብ ምንጭ ከሆኑት አለቆቻቸው ተለዋዋጭ ፍላጎት ጋር በየወቅቱ የተለያየ ቅርፅና መልክ ይዞ የሚተገበር ነው፡፡ ሌላ አስተያየት ሰጪ እንደገለፀው ፓርቲዎቹ በአባሎቻቸውና በህዝቡ ከመተማመን ይልቅ ከሃገር ውጭ ሆነው የሃገሪቱን እጣ ፈንታነሱ በሚመኙት መንገድ ለመዘወር በሚፈልጉ ግለሰቦች ተጽእኖ ስር የወደቁ ናቸው።
የትግል ስልታቸውም የተሻሉ የሚሏቸውን አማራጮቻቸውን ወደ ህዝቡ በማስረፅ ተቀባይነታቸውን እያሰፉ የመሄድ ሳይሆን የገዢውን ፓርቲና የመንግስትን ጥቃቅን የአፈፃፀም ጉድለቶችን አጉልቶና አዛብቶ በማቅረብ አመፅ እንዲቀሰቀስ የማድረግ አካሄድ በመከተል አለቆቻቸውን ማስደሰት ነው፡፡ የሚከተሉት የብጥብጥና የአመፅ አካሄድ እነሱ ላሰቡት ውጥን ትርፍ እስካስገኘ ድረስ በዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታው ላይ ለሚያሳድረው አሉታዊ ተፅዕኖ ብሎም በሀገሪቱ ለሚከሰቱ ጉዳቶች ደንታ የላቸውም፡፡

በአጠቃላይ በዴሞክራሲ ተቋምነት ስም በህጋዊ ፓርቲነት ተመዝግበው የተሰባሰቡ ነገር ግን በተግባራቸው ህጋዊና ህገ ወጥ መንገዶችን እያጣቀሱ የሚጓዙ የሀገራችን የፖለቲካ ፓርቲዎች ለዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታው እንቅፋት ስለመሆናቸው የእስካሁን መገለጫዎቻቸው በግልፅ ይመሰክራሉ፡፡ በአንፃሩ በሀገራችን ተግባራዊ እየተደረገ ለሚገኘው የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ዋነኛ ባለቤት የሆነው ህዝባችን ግን ከተቃዋሚ ፓርቲዎች ሁኔታ በተቃራኒ በእድገት ውስጥ ይገኛል፡፡ ፅንፈኛ ተቃዋሚዎች ህዝቡ ውስጥ ያልተረጋጋ ሁኔታ በመፍጠር በአመፅ እንዲሳተፍ ሲያደርጉት የነበረውን ሁኔታ አሁን ላይ አጀንዳቸውን በሚገባ ተረድቶ አግልሏቸዋል፡፡ የኢኮኖሚ፤ ማህበራዊ፤ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች ሲኖሩትም ጥያቄዎቹን አግባብነት ባለው መንገድ የሚያቀርብበትና የአጠቃላይ ሀገራዊ እድገቱ ባለቤት በመሆን ከምን ጊዜውም በላይ ሚናውን በሚገባ እየተወጣ ይገኛል፡፡

1 comment:

  1. opposition parties in have the following behaviors አማራጭ አስተሳሰብ የሌላቸው መሆን,የውስጠ ድርጅት ኢ ዴሞክራሲያዊነት,የጥላቻ ፖለቲካ አራማጆች መሆናው ,ለህዝብ ጥቅም ያልወገነ ተቃውሞ then .....

    ReplyDelete