EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Thursday 27 October 2016

ስለ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ምንነት

አለማችን በታሪክ አስከፊነታቸው ጎልቶ ከሚነገርላቸውሁለቱ የአለም ጦርነቶች በተጨማሪ በተለያዩ ጊዜያት በርካታ አስደንጋጭ ክስተቶችን አስተናግዳለች፡፡ በዘመናችንም ወረርሽኝ፤ የእርስ በርስ ጦርነት፤ ሽብርተኝነት፤ የጎርፍ፤ አውሎ ንፋስና መሬት መንቀጥቀጥ አደጋ በተለያዩ የአለማችን ክፍሎች ለሰው ሕይወት መጥፋትና ንብረት ውድመት ምክንያት ሲሆኑ ተመልክተናል፡፡

ሀገራት እነዚህ ክስተቶች ሲያጋጥሙ ወይም እንዳይከሰቱ ለመከላከል በተናጠልና በጋራ ብርቱ ጥረት ያደርጋሉ፡፡ በሃይቲ፤ በኔፓልና በጃፓን የተፈጥሮ አደጋዎች  በደረሱ ወቅት የሰውን ልጅ ከእልቂትና ጉዳት ለማዳን ሀገራት ተባብረዋል፡፡ በእርስ በርስ ጦርነት በሚታመሱ ሀገራት የሰላማዊ ዜጎችን ሕይወት ለመታደግ ሀገራት የሰላም አስከባሪ ኃይልን በማዋጣት ሃላፊነታቸውን ይወጣሉ፡፡ ወረርሽኝ በተከሰተ ጊዜም ባላሙያዎችንና ቁሳቁሶችን በመለገስ የተቻላቸውን ለማድረግ ይጥራሉ፡፡
የውጭ ሀገራት ቀውስና አደጋን ለመቀልበስ ከሚያደርጉት ትብብር በላይ ችግሩ የተከሰተባቸው ሀገራት የሚያጋጥማቸውን ቀውስ በራሳቸው ለመፍታትና የዜጎችን ሰላም ብሎም የሀገርን ህልውና ለማረጋገጥ የህግ ድንጋጌዎችን በመጠቀም ችግሮችን የመቅረፍ እርምጃ ይወስዳሉ፡፡ የተከሰተው ሰው ሰራሽም ሆነ የተፈጥሮ አደጋ የሀገርንና የህዝቡን ህልውና አደጋ ላይ የሚጥል ሆኖ ሲገኝ ሀገራት ከተለመደው አካሄድ ወጣ ያለ የህግ ድንጋጌ በማውጣት ችግሮችን የመቆጣጠር ጥረት ያደርጋሉ፡፡ ችግሮችን በተለመደው ህጋዊና አስተዳደራዊ አካሄድ ለመቆጣጠር የሚያስችል ሁኔታ በማይኖርበት ጊዜ ፈጣን ውጤት ለማምጣት የሚያስችል ድንጋጌ ወይም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተብሎ የሚጠራውን ሀገራት ስራ ላይ ያውላሉ፡፡
እስከአሁን በርካታ ሀገራት ይህንን የህግ ድንጋጌ የተገበሩ ሲሆን ግብጽ .. 1967 እስከ 2012 በአረብና እስራኤል ጦርነት ምክንያት በየሶስት ዓመት እየታደሰ በቀጠለው የረዥም ጊዜ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር ቆይታለች፡፡ የምዕራብ አፍሪካ ሀገራት የሆኑት ላይቤሪያና ሴራሊዮን 2014 ተከስቶ ለሺዎች እልቂት ምክንያት የሆነው የኢቦላ ወረርሽኝ ባጋጠመበት ወቅት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተግብረዋል፡፡
እየተገባደደ በሚገኘው የፈረንጆቹ 2016 የተለያዩ የአለማችን ሀገራት ባጋጠማቸው የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ምክንያት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተፈጻሚ አድርገዋል፡፡
አሜሪካ በቅርቡ በሰሜን አሜሪካ ካሮሊና ግዛት ቻርሎቴ በተባለው ከተማ በአንድ ጥቁር ግለሰብ ላይ ፖሊስ ሆን ብሎ ግድያ ፈጽሟል በሚል ጥቁሮች በተለያዩ ከተሞች ያደረጉት ተቃውሞ ወደ ግጭት በማምራቱ በተወሰኑ ከተሞች የተፈጠረውን አለመጋጋት ለመፍታት በሴፕቴምበር 2016 የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስራ ላይ ውሏል፡፡ የአሜሪካ ሌላኛዋ ግዛት በሆነችው ፍሎሪዳም ሃሪኬን ማቲው የተባለው አደገኛ የባህር አውሎ ንፋስ ባጋጠመበት ኦክቶብር 2016  የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ታውጇል፡፡ በተመሳሳይ በጁን 2016 በኦርላንዶ የምሽት ክበብ ላይ በተፈጸመ ጥቃት በደረሰው የሰው ህይወት መጥፋትና መቁሰል ምክንያት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተተግብሯል፡፡
በተጨማሪም በዚሁ ዓመት በቱኒዚያ፤ ማሊና በቬንዙዌላ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስራ ላይ ውሏል፡፡ በአሁኑ ወቅትም ፈረንሳይ፤ ቱርክና ኢትዮጵያ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር የሚገኙ ሀገራት ናቸው፡፡
በኖቬምበር 2015 በዋና ከተማዋ ፓሪስ ባጋጠማት የሽብር ጥቃት ምክንያት ፈረንሳይ ወዲያኑ ሀገር አቀፍ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መደንገጓ ይታወሳል፡፡ ፈረንሳይ ድርጊቱን ለመከላከል እስከ 2017 በሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር ትገኛለች፡፡ በቅርቡ የተቃጣባትን የመንቅለ መንስግት ሙከራ ያከሸፈችው ቱርክም በዋና ከተማዋ ኢስታንቡል ብቻ እስካሁን የዘለቀ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አውጃለች፡፡  በሀገራችንም በተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች ሰላምና ደህንነታችንን አደጋ ላይ የሚጥሉ ሁከትና ብጥብጦች መከሰታቸውን ተከትሎ ከመስከረም 28 ቀን 2009 . ጀምሮ ለስድስት ወራት የሚቆይ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተደንግጓል፡፡
የየሀገራቱ ተሞክሮ እንደሚያሳየው የዚህ የህግ ድንጋጌ ስራ ላይ መዋል አደጋው ጊዜ የማይሠጥና ተጽእኖው ቀላል አለመሆኑን እንዲሁም አፋጣኝ መፍትሄ የሚሻ መሆኑን የሚያመላክት ሲሆን አዋጁ እንደ አደጋው ስፋትና ጥልቀት በተወሰነ ቦታ ወይም በሀገር አቀፍ ደረጃ ሊታወጅ ይችላል፡፡
አንዳንዶች እንደሚሉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማስፈራሪያና ዜጎችን ተስፋ መቁረጥ ውስጥ የሚከት ሳይሆን የዜጎችን ደህነነት ለመጠበቅ ብሎም ህግና ስርዓትን ለማስከበር የሚረዳ የህግ ድንጋጌ ነው፡፡ የድንጋጌው ስራ ላይ መዋል መንግስት ተጨማሪ ህጋዊ አቅሞች ኖረውት አደጋው ተጨማሪ ጉዳቶችን እንዳያስከትል እንዲቆጣጠርና በአፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጥ ያስችላል፡፡ አዋጁን ስራ ላይ ማዋል የመንግስታትን ድክመትና ጥንካሬ የሚያሳይ ሳይሆን ስርዓቱን የሚፈታተን ድርስና ተጨባጭ አደጋ ሲኖር፤ አደጋውን በፍጥነት በመቀልበስ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን የሚያስችል መሆኑን ነው፡፡ ድንጋጌው ሀገራት የተጋረጠባቸውን አደጋ በመመከት ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እድገታቸውን ለማስቀጠል እንዲችሉ የሚረዳ መሳሪያም ጭምር ነው፡፡
በጥቅሉ ሲታይ የድንጋጌው ዓላማ ህገ መንግስታዊ ስርዓትና ህገ መንግስቱን ለመጠበቅ፤ በዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብቶች ላይ የተጋረጠ አደጋን በመከላከል ህግና ስርዓት እንዲረጋገጥ ማድረግ ሲሆን የተፈጥሮ አደጋ ሲያጋጥምም በአደጋው ጉዳት የሚደርስበት የህብረተሰብ ክፍል ከፍተኛ ኪሳራ እንዳይገጥመው ከመደበኛው ስርዓት ውጭ ተጨማሪ ኃብት በማቅረብ ችግሩ እንዲቀረፍ ይረዳል፡፡
ሀገራት ይህንን የህግ ድንጋጌ ለመደንገግ የተለያዩ አካሄዶችን የሚከተሉ ሲሆን በሀገራችን ወረራ ሲያጋጥም፤ ህገ መንግስታዊ ስርዓቱን አደጋ ላይ የሚጥል ሁኔታ ሲፈጠርና በተለመደው የህግ ማስከበር ስርዓት ችግሩን ለመፍታት ሳይቻል ሲቀር፤ የተፈጥሮ አደጋና የህዝብን ጤንነትን አደጋ ላይ የሚጥል በሽታ ሲያጋጥም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንደሚታወጅ በኢፌዴሪ ህገ መንግስት አንቀጽ 93 ሰፍሯል፡፡ በአንቀጹ መሰረት የፌዴራሉ መንግስት የሚኒስትሮች /ቤት አዋጁን የመደንገግ ስልጣን የተሰጠው አካል ሲሆን በክልሎች የተፈጥሮ አደጋ ሲያጋጥም ወይም የህዝብን ደህንነት አደጋ ላይ የሚጥል በሽታ ሲከሰት የክልል መስተዳድሮች በክልላቸው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ሊያውጁ ይችላሉ፡፡
በዚሁ መሰረት ላለፈው አንድ ዓመት ገደማ በተለያዩ የሀገራችን አካባቢዎች የተከሰቱት ችግሮች ሰላምና ጸጥታን ከማደፍረስ አልፈው በሰው ሕይወትና ንብረት እንዲሁም በአብሮነታችን ላይ የተጋረጠ አደጋ በመሆኑ ይህንን ለመቆጣጠርና አፋጣኝ መፍትሄ ለመስጠት እንዲቻል የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስራ ላይ ውሏል፡፡
በሚኒስትሮች /ቤት የሚደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተቀባይነት ለማግኘት የህዝብ ተወካዮች /ቤት በስራ ላይ ባለ ጊዜ 48 ሰዓታት ውስጥ፣ /ቤቱ በስራ ላይ ባልሆነበት ወቅት ደግሞ 15 ቀናት ውስጥ ቀርቦ 2/3 ድምጽ ማግኘት ይጠበቅበታል፡፡ በተጨማሪም ተቀባይነት ያገኘ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስራ ላይ የሚቆየው እስከ ስድስት ወራት ሲሆን የህዝብ ተወካዮች /ቤት  በየአራት ወሩ እንዲታደስ ሊያደርግ እንደሚችል በህግ መንግስታችን ሰፍሯል፡፡
በሚኒስትሮች /ቤት የሚደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በህገ መንግስቱ የተቀመጡትን የፖለቲካና የዴሞክራሲ መብቶችን መገደብ የሚችል ቢሆንም በምንም መልኩ በህገ መንግስቱ አንቀጽ 1 (የኢትዮጵያ መንግስት ስያሜ) 18 (ኢሰብዓዊ አያያዙ ስለመከልከሉ)25 (የእኩልነት መብት) እና 39 (1) እና (2) (የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች መብት) የተጠቀሱትን መብቶች የሚገድብ ሊሆን እንደማይችል ተደንግጓል፡፡ በሀገራችን የታወጀው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅም እነዚህን የህገ መንግስቱን ድንጋጌዎች በሙሉ መሰረት ያደረገና ያከበረ ነው፡፡

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሰላምና መረጋጋት ለማስፈን፤ የዜጎችን ደህንነት ለማረጋገጥ፤ የኢኮኖሚ አውታሮችና ኢንቨስትመንቶችን ከጥቃት ለመጠበቅ እንዲሁም አጥፊዎችን ለህግ በማቅረብ ረገድ የጸጥታ ሓይሎች ተቀናጅተው እንዲሰሩ አስችሏቸዋል፡፡ በዚህም ዜጎች  የእለት ተዕለት ተግባራቸውን ያለስጋት ማከናወን እንዲችሉ፤ የመማር ማስተማር ሂደት በሰላማዊ መንግድ እንዲከናወንና ሰራተኞችና ተቋማትም በምርትና ምርታማነት ላይ እንዲያተኩሩ ረድቷል፡፡

No comments:

Post a Comment