EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Tuesday 10 January 2017

በትጋታችን ያገኘንው ውጤት

(በኤፊ ሰውነት)
እንደሚታወቀው 2007. ጀምሮ በተፈጠረው የኤልኒኖ ክስተት ምክንያት ኢትዮጵያን ጨምሮ በርካታ የዓለም አገራት በአየር ንብረት መዛባት ተፅእኖ ስር እንዲወድቁ የተገደዱበት ሁኔታ ተፈጥሯል፡፡ ይህ በአገራችንም የክረምት ዝናብ ላይ ተፅእኖ ያሳደረ ሲሆን በተለይ በመኸር አብቃይና በአርብቶ አደር አካባቢዎች ከፍተኛ የሆነ ጫና አሳድሯል፡፡ የበልግ ዝናብ ባለመስተካከሉና የክረምት ዝናብም በኤልኒኖ ክስተት ምክንያት ተፅእኖ ስር በመውደቁ በአገራችን በምግብና መሰል ጉዳዮች ላይ ችግር መፈጠሩ ይታወሳል፡፡ በመኸር አብቃይና በአርብቶ አደር አካባቢዎች ላይ የዝናቡ ሁኔታ በመዛባቱ በግብርና ምርት፣ በውሃ፣ በጤና፣ በትምህርት ልማት ስራዎች፣ በምግብና ስነ ምግብ ዘርፎች ላይ ከፍተኛ የሆነ አሉታዊ ተፅእኖ ያሳደረበት ሁኔታ ፈጥሮ ነበር፡፡ በወቅቱ በአገራችን የእለት ደራሽ እርዳታ ፈላጊዎች ቁጥር 2007 ነሃሴ ወር ከነበረበት 4 ነጥብ 5 ሚሊዮን 2008 ጥር ወር ወደ 10 ነጥብ 2 ሚሊዮን አድጎ ነበር፡፡

በአየር ንብረት መዛባት ምክንያት የተፈጠረው ይህ ችግር በአገራችን የተከሰተውን ድርቅ ከበርካታ ዓመታት ወዲህ ትልቁና የከፋው አድርጎታል፡፡ ይሁንና ሀገራችን ባደረገችው ከፍተኛ ጥረት በተለይ ባለፉት ዓመታት የተደረገው ሁሉን አቀፍ ስኬታማ የልማት እንቅስቃሴ የድርቅ አደጋው የከፋ ጉዳት ሳያደርስ ትርጉም ባለው መልኩ ለመከላከል ተችሏል፡፡ በም/ጠቅላይ ሚንስትሩ የሚመራውን የብሔራዊ አደጋ መከላከልና ዝግጁነት ኮሚቴ እንደገና በማጠናከርና አሰራሮችን በማሻሻል፤ አብይ ኮሚቴና የቴክኒክ ኮሚቴውንም በማጠናከር የአንድም ሰው ህይወት እንዳይጠፋ እረፍት የለሽ እንቅስቃሴ በማድረግ ስኬታማ ተግባራት ማከናወን ተችሏል፡፡ የተረጂዎችን ቁጥር ከመለየት ጀምሮ የሚያስፈልገውን በጀት በመወሰንና የመፍትሄ አቅጣጫዎችን በማስቀመጥ ወደ ተግባር በመገባቱም ነው በሰው እና በእንስሳት ላይ የከፋ አደጋ ከመድረሱ በፊት መቆጣጠር የተቻለው፡፡  
በዋነኝነት በራሳችን የውስጥ አቅም ችግሩን ለመቆጣጠር የተሄደበት ርቀት ባለፉት ዓመታት በአገራችን የተመዘገበው እድገት ምን ያህል ዓቅም እንደፈጠረልን የሚያሳይ ነው፡፡ ለተረጂዎች የሚውል 1 ነጥብ 12 ሚሊዮን ሜትሪክ ቶን ስንዴና 50 ሺህ ሜትሪክ ቶን አልሚ ምግብ ከውጭ ተገዝቶ በወቅቱ ጥቅም ላይ እንዲውል ማድረግ ተችሏል፡፡ በአገር ውስጥ ደግሞ በቆሎ፣ ማሽላ፣ ጥራጥሬ፣ አልሚ ምግብና ዘይት ተገዝቶ ቀርቧል፡፡ በሂደቱም የፌዴራል መንግስት ብቻ 16 ነጥብ 5 ሚሊዮን ብር ወጪ አድርጓል፡፡ የክልል መንግስታት የግል ባለሃብቱና ህብረተሰቡ ያወጡት ሲደመር ደግሞ ድርቁን ለመቆጣጠር ምን ያህል የራሳችንን አቅም መገንባት እንደቻልን የሚያመላክት ነው፡፡ በጥቅሉ አገራችን ባለፉት ዓመታት ያስመዘገበቸው ሁሉን አቀፍ ለውጥ መንግስት በቂ ሃብት በመመደብ ማንንም ሳይጠብቅ ለህዝባችን ምላሽ ለመስጠት እንዳስቻለው መገንዘብ ይቻላል፡፡ ይህ ክስተት ካለፍናቸው የታሪክ ምዕራፎች አኳያ አንፀባራቂ ድል ተደርጎ የሚወሰድ አኩሪ ተግባር ነው፡፡
መንግስትን ጨምሮ ሁሉም የአገራችን ህዝብና የክልል መንግስታት እንዲሁም የግል ባለሃብቶች በጋራ ተረባርበው በአገራችን የተከሰተውን የድርቅ አደጋ መከላከልና መቆጣጠር መቻላቸው 2008 ግንቦት ወር ኢስታንቡል ላይ በተደረገው የአለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ጉባኤ ላይ አገራችን ልምዷን እንድታካፍል ተደርጋለች፡፡
በአሁኑ ወቅት የዕለት ደራሽ እርዳታ ፈላጊዎች ቁጥር ወደ 5 ነጥብ 6 ሚሊዮን ወርዷል፡፡ ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስታችን ማናቸውንም አደጋዎች መቋቋም የምንችለው የውስጥ አቅማችንን በመገንባት መሆኑን በፅናት ያምናል፡፡ ለዚህም ከሁሉም አስቀድመን ድህነት ላይ የምናደርገው ሁሉን አቀፍ ርብርብ መጠናከር እንደሚገባው በግልፅ ያስቀምጣል፡፡ ትናንት እንኳንስ ይሄን ያህል ቁጥር ያለው ህዝብ ለድርቅ አደጋ ተጋልጦ ይቅርና ትንሽ ቁጥር ያለውን የአንድ አካባቢ ህዝብ እንኳን በራስ ዓቅም በአደጋ ጊዜ መደገፍ የሚቻልበት እድል ፈፅሞ አልነበረም፡፡ ይህም በአንድ በኩል ኢኮኖሚው ያን ያህል ችግር የመቋቋም አቅም ስላልነበረው በሌላ በኩል ደግሞ መንግስታቱ ያን ያህል ኃላፊነት ለመሸከም የሚያስችል ቁመና ስላልፈጠረባቸው እንደሆነ ለማናችንም ግልፅ ነው፡፡ በዚህም በየወቅቱ በተከሰቱ ድርቆች አማካይነት የዜጎቻችን እጣ ፈንታም ሞት ብቻ የነበረበትን ሁኔታ እንደነበረ ማስታወስ ይቻላል፡፡
ዛሬ ፊታችንን ወደ ልማት ማዞራችንና መስመራችንን ድህነት ተኮር ማድረጋችን ዓለም ጭምር የተደመመበትን ለውጥ ማስመዝገብ አስችሎናል፡፡ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ሳይቀር በአገራችን ተከስቶ የነበረውን ድርቅ ስፋት በመዘገብ ሁኔታውን ይከታተሉት የነበረና ተግባራዊ ምላሻችንን ያደነቁበት ነው፡፡ ዛሬ ላይ ደግሞ አደጋውን ከመከላከል አልፈን የተረጂዎችን ቁጥር በማውረድ አንድ ርምጃ ወደ ፊት መጓዝ ተችሏል፡፡ ይህ በልማታዊ መንግስታችንና በህዝባችን ያላሰለስ ጥረት የተገኘ ድል በመሆኑ ነገም በጸረ ድህነት ላይ የምናደርገውን እልህ አስጨራሽ ትግል በስኬት ለመወጣት በአንድ ልንተም ይገባል፡፡
የብሔራዊ አደጋ መከላከልና ዝግጁነት ኮሚቴ ሰሞኑን ባደረገው ስብሰባ የኢፌዴሪ ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር አቶ ደመቀ መኮንን እንደገለፁት ባለፈው ዓመት የነበረውን ድርቅ ለመቆጣጠር ቢቻልም አሁንም ከዛ ተሻጋሪ ከሆነው ተፅእኖ በሁሉም አካባቢዎች ገና ያልተላቀቅን በመሆናችን የዞረ ሂሳብ እንዳለብን አስበን መረባረብ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ አቶ ደመቀ አያይዘውም እያረጋገጥን ያለነው የእድገት መንገድ አደጋውን ለመሸከም እንዳስቻለን በመግለፅ ዘላቂነቱን ለማረጋገጥ ግን በቀጣይነት መረባረብ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
የልማት አጋሮቻችን የአደጋውን ስፋትና ጥልቀት ያህል ባይሆንም ቀላል የማይባል ድጋፍ ማድረጋቸውን የጠቆሙት ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩ ህብረተሰቡና የግል ባለሃብቱ ያደረጉትን አስተዋፅኦን አድንቀዋል፡፡ በመንግስት የሚደረጉ ሌሎች ድጋፎችም ዘላቂ እድገት የሚያመጡ እንዲሆኑ እንደሚሰራም አመላክተዋል፡፡
በአገራችን የተከሰተውን ድርቅ ለመቋቋም በተሰሩ ስራዎች የተገኙ ውጤቶች ይበል የሚያሰኙ ናቸው፡፡ ሁሉም ዜጋ ከመንግስት ጋር በመሆን ከዚህ በላይ ርብርብ ቢያደርግ ደግሞ ከዚህ በላይ አቅም መገንባት እንደሚቻል ከባለፈው ልምዳችን ተነስተን መደምደም እንችላለን፡፡ እናም ሁላችንም የቻልነውን ያህል ልማታዊ አስተዋፅኦ በማበርከት ሁሌም ቢሆን ችግሮቿን በራሷ የውስጥ አቅም መቋቋም የምትችል የማትበገር አገር ለመፍጠር መረባረብ ይኖርብናል፡፡

No comments:

Post a Comment