EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Saturday 25 August 2018

ለውጡ በነውጥ ሴራና ለእኩይ ተግባር በሚሰራጭ ገንዘብ ሊገታ አይችልም!!


በአሁኑ ጊዜ በሀገራችን ኢትዮጵያ ለዘመናት ስር ሰዶ የቆየው የጥላቻና ቂም በቀል የፖለቲካ ምዕራፍ የሚዘጋበት፤ በምትኩ የይቅርታ፣ የፍቅርና የአብሮነት ፖለቲካዊ ሁኔታ የሚፈጠርበት ስር ነቀል የለውጥ ጉዞ ተጀምሯል። ይህ ሀገራዊ የለውጥ ጉዞ በሀገራችን ኢትዮጵያ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ የታየ፤ በአይነቱም ሆነ በይዘቱ በእጅጉ የተለየና መላውን የሀገራችንን ሕዝቦች በተስፋና በአንድነት ጎን እንዲሰለፉ ያደረገ ነው።
የለውጥ ጉዞው በአጭር ጊዜ ሀገራችንን ገጥሟት ከነበረው ያለመረጋጋት እና የሰላም እጦት የታደጋት ከመሆኑም ባሻገር በሕዝቦቿ ዘንድ ተፈጥሮ የነበረውን የፍርሃትና የጥርጣሬ ስሜት በመግፈፍ ለዘመናት ተሸርሽሮ የነበረው ሀገራዊ አንድነታችን እንዲጠናከር ጉልህ ሚና ተጫውቷል።
ከዚህ በተጨማሪ ለውጡን በተግባር በመቀየር የሀገራችን ሕዝቦች ሲያነሱት የነበረውን የዴሞክራሲና ሰብዓዊ መብቶች አያያዝ ችግር ለመቅረፍ እንዲሁም የልማትና መልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ለመፍታት ምልዓተ ሕዝቡን ባሳተፈ መልኩ ሰፋፊ እንቅስቃሴዎች በመደረግ ላይ ይገኛሉ።
የተጀመረው ሀገራዊ ለውጥ በመላ የሀገራችን ሕዝቦች ዘንድ ከፍተኛ ተስፋ ያሳደረ ቢሆንም ከለውጡ የማይጠቀሙ ይልቁንም ጥቅማቸው በቀጥታ የሚነካ ኪራይ ሰብሳቢ ግለሰቦችና ቡድኖች ዛሬም ልክ እንደተለመደው በጥቅም በታወረ አስተሳሰብ የሀገርንና የሕዝብን ፍላጎት ወደ ጎን በመተውና ራሳቸውን ብቻ ማዕከል በማድረግ ለውጡን ለማዘግየት ከተቻላቸውም ለመቀልበስ ባለ በሌለ ሃይላቸው የአፍራሽ ሴራቸውን እያራመዱ ይገኛሉ።
ይህ ስብስብ ባለፉት ጊዜያት የመንግስት ስልጣንን ተጠቅሞ የብሔር እና የሕገ መንግስት ጭንብል ለብሶ የሀገር እና የሕዝብ ገንዘብ ሲዘርፍ የነበረና አሳፋሪ ተግባር ሲፈፅም የኖረ ስለሆነ የተጀመረው ለውጥ ተጠናክሮ ከቀጠለ የሰረቀውን እንዳይመልስና በህግ እንዳይጠየቅ ስለሚፈራ የተካነበትን እኩይ ተግባር ተጠቅሞ ለውጡን ለማጠልሸትና ብዥታዎችን ለመፍጠር እየሰራ ይገኛል። ይሁንና የተጀመረው ሀገራዊ የለውጥ ጉዞ በሕዝባችን ፍላጎት፣ ባለቤትነትና ሁለንተናዊ ተሳትፎ የሚካሄድ በመሆኑ ጥቂቶች በሚጠነስሱት የነውጥ ሴራና ለጥፋት በሚሰራጭ ገንዘብ ለአፍታም ቢሆን ሊገታ አይችልም።
የተጀመረውን ሀገራዊ የለውጥ ጉዞ አጠናክሮ የማስቀጠል ጉዳይ የመሪ ድርጅታችን ኢሕአዴግ፣ የሀገራችንና የሕዝቦቿ የህልውና ጉዳይ በመሆኑ ለውጡን ለማደናቀፍ የሚጣጣሩ ሃይሎች ከዚህ እኩይ ተግባር መቆጠብ የሚገባቸው ይሆናል። መላው የሀገራችን ሕዝቦችም በትግላቸው የጀመሩትን የለውጥ ጎዳና ያለእንከን ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሸጋገር እያደረጉ ያሉትን ድጋፍ አጠናክረው መቀጠልና ይህን ለማደብዘዝ የሚጥርን ማንኛውም ተግባር በፅኑ መታገል ይኖርባቸዋል።

No comments:

Post a Comment