EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Friday 30 March 2018

በርካታ ልዩነቶች ቢኖሩንም በኢትዮጵያችን አንድ ነን!



አደም ሀምዛ
ኢትዮጵያችን አሁን ላይ ሀገራዊ ኢኮኖሚዋን በዓመት በአማካይ በሁለት አሃዝ የእድገት ምጣኔ በማሳደግ በተጨባጭ ፈጣን ኢኮኖሚያዊና ዘርፈ ብዙ ሀገራዊ እድገት በማስመዝገብ በአዲስ የህዳሴ ምዕራፍ እየተጓዘች ትገኛለች፡፡ የሀገራችን ፈጣን የእድገት ግስጋሴ ከምንጠብቀው የብልፅግና ግብ አንፃር ገና በሂደት ላይ የሚገኝና በዜጎች ሰፊና የነቃ ተሳትፎ ረጅም ርቀት መጓዝ የሚኖርበት ቢሆንም የእስካሁን ውጤቶቹ ስኬታማነቱን በግልፅ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ይህን እውነታ እራሳችን ከመመስከርም አልፎ የሀገራችን ፈጣንና ተከታታይ እድገት በርካታ ሀገራትን ጨምሮ በተለያዩ አህጉራዊና አለማቀፋዊ ተቋማትና እንዲሁም በምጣኔ ሃብትና መሰል የሙያ ዘርፎች ላይ ጥናትና ምርምር በሚያደርጉ ታዋቂ ግለሰቦች ዘንድ ታላቅ እውቅናና አድናቆትም እያገኘ ይገኛል፡፡ በተመሳሳይ እነዚህ ተቋማትና ግለሰቦች የሀገራችንን ፈጣንና ስኬታማ እድገት ከማሞገስም ባለፈ በተለይም በአንዳንድ ዘርፎች ያስመዘገብነው ስኬታማ ሀገራዊ የእድገት ተሞክሮን በበርካታ መድረኮች ላይ ለሌሎች መሰል ሀገራትም የእድገት አማራጭ ተሞክሮ ሆኖ እንዲያገለግል እንዲሁ ምክረ ሀሳባቸውን እንዲሰጡ እያደረገ ይገኛል፡፡
በአጠቃላይ የእድገት ስኬታማነታችን ከሚያገኘው እውቅናና አድናቆትም በተጨማሪ በርካታ ሀገራትንና አለም አቀፍ የፋይናንስና የኢንቨስትመንት ተቋማትን የልማት አጋር በማድረግ ቀጥታ የውጭ ኢንቨስትመንት ወደ ሀገር በመሳብ የንግድና የገበያ ትስስር በከፍተኛ መጠን እየፈጠረ ለመሆኑ ሌላኛው የሚታይ  እውነታ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህም በታዳጊ ደረጃ ላይ የሚገኘው ሀገራዊ እድገታችን እስካሁን ባልፈታቸው የዜጎች የልማት ጥያቄዎች ብቻ በመታጠር ችግሮችን በማጉላት የእስካሁን ስኬችን የሚክዱም ይሁን ቀጣዩን የሀገሪቱንና የዜጎቿን የእድገት ተስፋ በጨለምተኝነት የሚያዩና እንዲታይ የሚሹ አካላትን ለትልቅ ትዝብት በመዳረግ በሀገር ውስጥና በውጪ በተለያዩ ሀገራት በሚኖሩ ዜጎችና በአለምአቀፉ ማህበረሰብ ተዓማኒነት እንዳይኖራቸው ያደረገ ነው፡፡  
አስቀድመን ከምንታወቅበት እጅግ ኋላቀር የኢኮኖሚ ስርዓትና አስከፊ የድህነት ሁኔታ ፈጥነን ለመውጣት ላለፉት ሁለት አስርተ ዓመታት በላይ ኢህአዴግ በሚከተለው ዴሞክራሲያዊና ልማታዊ የፖለቲካ ስርዓት እና ድርጅትታዊ የአመራር ፍልስፍና እየተመራን በተለይ በመጨረሻዎቹ 15 ዓመታት በተከታታይ እየተመዘገበ በሚገኘው ባለሁለት አሃዝ ፈጣን የእድገት ምጣኔ አማካኝነት ዘርፈብዙ እድገቶችን በኢኮኖሚውና በማህበራዊ መስኮች እያስመዘገብን በህዳሴ ጉዞ ላይ እንድንገኝ አስችሎናል፡፡ ከእነዚህ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ እድገቶች በተጨማሪ ከምንገኝበት ከምስራቅ አፍሪካ ያልተረጋጋ የሰላም፣ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ቀውስ ቀጠና በተለየ ሁኔታ በሀገራችን ከጅምሩ አንስቶ አስተማማኝና ዘላቂ ሰላም እንዲሰፍን እና የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ ስርዓት ዋስትና እንዲያገኝ ለማድረግ ተችሏል፡፡
ከእስካሁኑ የሀገራችን የህዳሴ ጉዞ በመነሳት በአንድ በኩል እየተመዘገቡ በሚገኙ የለውጥና የእድገት የልማት ድሎች በርካታ የሀገሪቱን ዜጎች ከነበሩበት አስከፊ ድህነት በማላቀቅ ተጠቃሚ እያደረጋቸው ሲሆን የዜጎችን የልማትና የእድገት ተደራሽነት በአይነትና በመጠን በማስፋት እንደ ሀገር ጠንካራና ተወዳዳሪ የኢኮኖሚና የዴፕሎማሲ አቅም እያጎናጸፉን በመሄድ ላይ ይገኛሉ፡፡ በሌላ በኩል እንደሀገር አሁን ላይ በግንባታ ሂደት ላይ የሚገኙና በቀጣይ ተጠናቀው መላ ህዝባችንና ሀገራችንን በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ተጠቃሚ ማድረግ ከሚችሉ በርካታ ሰፋፊ ሀገራዊ የልማት ፕሮጀክቶች ከሚፈጥሩት ተጨማሪ የልማት አቅም ጋር የሀገራችን የህዳሴ ጉዞ በተስፋ የተሞላና ማንኛውም ዜጋ ይህን እውን ሆኖ ማየትን እንዲጓጓ የሚያደርግ እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡
በስኬት እየተጓዘ የሚገኘውና ፍፃሜውንም ለማየት አጓጊ የሆነው የሀገራችን የህዳሴ ጉዞ ከላይ ከገለፅናቸው አዎንታዊ እውነታዎች በተጨማሪ እንደሀገር ከውስጣችን ከሚፈጠሩና ከውጭም ከምንገኝበት ከምስራቅ አፍሪካ ያልተረጋጋ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ቀጠና አንስቶ ተለዋዋጭና ውስብስብ አለም አቀፋዊ ሁኔታዎች በሚያስከትሉት አሉታዊ ተፅዕኖዎች በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ ህዳሴያችንን የሚያጨልሙ በርካታ ተግዳሮቶች መኖራቸውንና በቀጣይም ውስብስብና ተለዋዋጭ ባህሪያቸውን ይዘው ሊቀጥሉ እንደሚችሉ በሚገባ መገንዘብ ተገቢ ይሆናል፡፡
እነዚህ ምንጫቸው ከውስጥና ከውጭ ሊሆን የሚችል ሀገራዊ ስጋቶችና ተግዳሮቶች በአይነትና በመጠን እንዲሁም በውስብስብ ባህሪያቸውና በተፅዕኖ ደረጃ የሚኖራቸው መለያየት እንደተጠበቀ ሆኖ አስቀድመውም የነበሩና በቀጣይም ተለዋዋጭ ባህሪያቸውን ጠብቀው እንደወቅቱ ሁኔታ በሀገራችን ሊከሰቱ መቻላቸው በተመሳሳይ ቀጣዩን የህዳሴያችን ጉዞ ስኬታማነት ለማስቀጠል የሚደረገውን ሀገራዊ ትግል እንዲሁ ከባድና ውስብስብ እንዲሆን ያደርገዋል፡፡
ኢህአዴግ እንደሀገር ለሚፈጠሩ በተለይም ለውስጥ ችግሮቻችን ቅድሚያ በመስጠት በአይነትና በመጠን ለይቶ በቂና ጥልቅ ትንታኔ በማድረግ እንደወቅቱ ሁኔታ ሳይንሳዊና ድርጅታዊ መፍትሔ እየሰጠ፣ ከጠንካራ ክትትልና ግምገማ መነሻ ቀጣይነት ያለው ርብርብ ማድረግ ውስጣዊ ችግሮቻችንን በሚገባ ለመቅረፍ ከማስቻል አልፎ ሀገራዊ ተጋላጭነትን በአስተማማኝ መቀነስና ከፍ ባለ ደረጃሌሎች ውጫዊ ተግዳሮቶችን አደጋ መመከት ያስችላል የሚል ጠንካራ እምነት በመያዝ ባደረጋቸው እንቅስቃሴዎች እንደሀገርና እንደመሪ ድርጅት በርካታ ስኬቶችን በመጎናፀፍ ለህዝቡ በተግባር ጭምር የመፍትሔ ድርጅት እንደሆነ በሚገባ አሳይቷል፡፡
ኢህአዴግ የሀገሪቱንና የህዝቡን የረጅም ጊዜ ምኞት የነበረውን ዴሞክራሲያዊና ልማታዊ የመንግስት አስተዳደር ገና ከጅምሩ እውን በማድረግ በሁሉም ዘርፎች እድገትና ስርነቀል ለውጥ እንዲመጣና እንደድርጅት ፖለቲካዊ ቁመናው እንዲገነባ በማድረግ ረጅም ርቀት እየተጓዘ ቢሆንም በሌላ በኩል በርካታተቃዋሚ ፓርቲዎች የዚህ ሀገራዊ ለውጥ ባለቤት በመሆንና የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ ስርዓቱ እንዲጠናከር የነበራቸው አስተዋፅኦ ጎልቶ የሚታይ አልነበረም፡፡ በተቃራኒው እንደድርጅት ጠንካራና ተወዳዳሪ በመሆን ለህዝቡ አማራጭ በመሆን ከመቅረብና በተለያዩ ሀገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ ፖለቲካዊ ትግል በማድረግ ሀገራዊ አስተዋፅኦ ከማበርከት ይልቅ ለሚያጋጥማቸው የውስጥ ችግር ጭምር ድርጅታዊ መፍትሔ መስጠት ተስኗቸው ሲፍረከረኩና ሲበተኑ ችግሮቻቸውን በተደጋጋሚ ውጫዊ በማድረግና አልፎም አንዳንዶቹ ኢህአዴግን ጭምር ለዚሁ ተጠያቂ በማድረግ ወቀሳ ሲያቀርቡ የሚስተዋሉ ናቸው፡፡
በአጠቃላይ የሀገራችን ተቃዋሚ ፓርቲዎች ጥንካሬና ዴሞክራሲያዊነት ያለመጎልበት እንደፓርቲ ከራሳቸው ባለፈ እንደሀገር ሁሉንም ተጠቃሚ ለሚያደርገውና ከጅምሩ አንስቶ በውጤቶቹ በርካቶችን ተጠቃሚ ማድረግ የጀመረውን ሀገራዊ የእድገትና የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታ ጉዞ ረጅም ርቀት እንዲጓዝና ጠንካራ ሀገራዊ መግባባት እንዲፈጠር በማድረግ የሚጠበቅባቸውን ሀገራዊ ኃላፊነት በሚገባና በሰለጠነ አግባብ ማበርከት እንዳይችሉ አድርጓል፡፡ በሀገራችን የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ ስርዓት እውን መደረግ ከጀመረ ከሁለት አስርተ ዓመታት ቢቆጠርም የፖለቲካ ድርጅቶች በተናጠል ፖለቲካዊ አቅምና ቁመና በመፍጠርም ይሁን እንደሀገር በመካከላቸው የእርስ በእርስ መስተጋብር በመፍጠር ጠንካራ ሀገራዊ መግባባት ለመፍጠር የደረሱበት ቁመና የእድሜውን ያህል ያላደገና በበርካታ ችግሮች የታጠረ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡
ለዚሁ ነው በሀገራችን የሚገኙ ሁሉም የፖለቲካ ፓርቲዎች ሁሌም ፖለቲካዊ የሀሳብ ልዩነቶቻቸው እንደተጠበቁ ለሀገርና ለህዝብ ጥቅሞች ቅድሚያ ትኩረት በመስጠትና በትልቅ ሀገራዊ ኃላፊነት ተልዕኳቸውን በሚገባ ፈጥነው ተግባራዊ ሊያደርጉ እንደሚገባ ማስገንዘቡ አስፈላጊ የሚሆነው፡፡ ሁሉም የሀገራችን የፖለቲካ ድርጅቶች ከምንምና ከማንም በላይ ቅድሚያ ለዜጎችና ለሀገር ጥቅም ብቻ በመስጠት በተናጠል እንደድርጅትም ይሁን እንደሀገር እርስ በእርስ በመካከላቸው የሚያደርጉት ትክክለኛ መርህንና ህጋዊ አካሄድን መሰረት ያደረገ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴና ትግል ጠቀሜታው ከፍተኛ ሲሆን በተለይም አሁን ላይ ካጋጠመው አለመረጋጋት ጋር ተያይዞ ለሀገራችን ከሚኖረው ጉልህ ሚና አንፃር ወቅታዊና ትልቅ ጉዳይ ተደርጎ የሚወሰድ ይሆናል፡፡
ከዚህ አንፃር እንደሀገር ከቅርብ ጊዜ አንስቶ የተጀመረውና በፖለቲካ ፓርቲዎች መካከል ተቀራርቦ ለመስራትና በሰለጠነ አግባብ በመካከላቸው የሚኖሩ ፖለቲካዊ የሃሳብ ልዩነቶችን በክርክርና በውይይት ትግል ለማድረግ እየተሞከረ ያለውን ጥረት በተሻለ ጥንካሬ ለማስቀጠልና ወደ ውጤት ለማሸጋገር ሁሉንም ህጋዊ ፓርቲዎች አባል ሆነው እንዲቀጥሉ ከማድረግ አንስቶ ሌሎች አስፈላጊነት ያላቸውን እርምጃዎች በመለየተ ተግባራዊ እንዲሆኑ በሁሉም ዘንድ ተገቢው ርብርብ ሊደረግ ይገባዋል፡፡ በዚህም በወቅታዊነት ያለንበትን ሀገራዊ አለመረጋጋት በዘላቂነት እንዲፈታ እየተደረገ ያለውን ጥረት ለማገዝና እንደድርጅት በርካታ፣ ጠንካራና ሀገራዊ ተወዳዳሪ ፓርቲመፍጠር ጠንካራ መሰረት ለመጣል ተጨማሪ ሀገራዊ አቅም እንዲፈጠር ከማድረግ ባለፈ በጊዜ ሂደት እንደሀገር ጠንካራ የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲንና ሀገራዊ መግባባትን መገንባት ያስችላል፡፡
እንደሀገር ካለንበት የሁከትና ያለመረጋጋት ሁኔታ በዘላቂነት ለመውጣትና ቀጣይነት ያለው ሀገራዊ መግባባት እየተገነባ እንዲሄድ ትልቅ ድርሻ የሚጫወተውን ምክንያታዊ ዜጋ በተለይም በወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ዘንድ መፍጠር ወሳኝ ነው፡፡ የጥፋት ኃይሉ በርካታ የህብረተሰብ ክፍሎችን በተለይም ወጣቱን ፍፁም ስሜታዊ እንዲሆን አድርጎ በማነሳሳት እንደሀገር የምንታወቅበትን ብዝሃነታችንን ተከትሎ ለረጅም ዘመናት አብሮ የኖረውን ተከባብሮ የመኖር ጠንካራ እሴቶችን በሚንድ አግባብ በብሔሮች መካከል ቁርሾ በማስነሳትና እርስ በእርስ በማጋጨት  የንፁኋን ዜጎች ህይወት እንዲቀጠፍና የአካል ጉዳት እንዲደርስ ከማድረግ አንስቶ በርካታ የሀገርና የህዝብ ሃብትና ንብረት ውድመት አሁን ላይ እየሆነ ያለውን ጨምሮ በተለያዩ ወቅቶች እንዲከሰቱ የሚያደርጉ ተግባራት እንዲፈፀሙ በማድረግ ላይ ነው፡፡
በሀገራችን አሁን ላይ በተጨማጭና በግልፅ እየታየ ያለው የዜጎችን ህይወት እያጠፋና አካል እያጎደለ እንዲሁም ሀገራዊ የኢኮኖሚ እድገታችን በዝቅተኛና በጀማሪ ደረጃ ላይ ያለ ከመሆኑ ጋር በተያያዘ በርካታ የህብረተሰቡ የልማት ጥያቄዎች በአግባቡ ባለተመለሱበት ሁኔታ ከፍተኛ መጠን ያላቸውን የህዝብንና የግለሰቦችን ሀብትና ንብረት እያወደመና ከአገልግሎት ውጪ እያደረገ ያለ የጥፋት ኃይሎች ተልዕኮና ተግባሩ ጥፋት ውጤቱም ጉዳትና ተጎጂ ብቻ የሆነ የኋልዮሽ ጉዞን የሚያከትል የዜሮ ድምር ብቻ ሳይሆን አሁን ላይ እንደሀገርና ህዝብ ለደረስንበት ተጨባጭ እውነታ ፍፁም የማይመጥነን፣ አወዳሚና የከሰረ የፖለቲካ ጫዋታ ነው፡፡
እውነታው ይህ ሆኖ ሳለ ታዲያ ይህን ሁሉ ጥፋት እንደሀገር ለምን ፈቀድን ስንል የምናገኘው እየሆነ ያለው ሁሉ በምክንያታዊነት መሆኑ ቀርቶ እይታችንን እንደሀገር ሳይሆን ግላዊና ቡድናዊ አድርገን በመጥበብ በስሜታዊነት እየተመራን መሆኑ ነው፡፡ ስሜታዊነት በግለሰብ ደረጃ እንኳ ምን ያህል ጉዳት እንዳለው ሁላችንም በሚገባ የምናውቀው ሆኖ ሳለ እንደሀገር ይህንኑ አስተሳሰብ ይዘን ወዴትስ መዝለቅ ይቻለናል ብለን ሁላችንም እንደዜጋ ከግለሰብ እስከ ፖለቲካ ድርጅት ያለን አካላት እራሳችንን በመጠየቅ እንደሀገር ከተደቀነብን አደጋ ለመላቀቅ ወደ መፍትሔ የሚያደርሰንን መንገድ ልንቀይስ ይገባል፡፡
በተለይም የሀገራችን የፖለቲካ ድርጅቶች ከዚህ አንፃር አሁን ላይ ሀገሪቱ ከባድ የቤት ስራ እንደሰጠቻቸው በሚገባ ተረድተው እርስ በእርስ ያላቸውን የፖለቲካና የአስተሳሰብ ልዩነት በቀጣይም ሊኖር እንደሚችልና አለማዊ እውነታ ጭምር መሆኑን ተረድተው እንደፓርቲ ጉድለቶቻቸውን በመቅረፍና በጋራ አብሮ በመስራት ሀገሪቱንና ህዝቦቿን ካጋጠማቸው ወቅታዊ አደጋ ለመታደግ ከፍተኛ ጥረት ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ የፖለቲካ ፓርቲዎች መላ ህዝቡን ከስሜታዊነት ነፃ ሆኖ ጥያቄቹም በምክንያታዊነት እንዲያቀርብና ከጥፋት ተግባራት እንዲቆጠብ በማድረግ ትልቅ ኃላፊነት ጭምር እንዳለባቸው ተረድተው አስፈላጊውን እንቅስቃሴ ሊያደርጉ ይገባል፡፡ በርካታ ልዩነቶች ቢኖሩንም ሁላችንም ያለን አንድ ሀገር ብቻ በመሆኑም ሀገራችንን ከጥፋት የመጠበቅ ኃላፊነት የሁላችንም ሊሆን ይገባል፡፡

No comments:

Post a Comment