EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Friday 20 January 2017

በጋራ ጥረት የሚሳካ አበረታች እንቅስቃሴ


(በኤፊ ሰውነት)
በአገራችን የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ እውን መሆን የጀመረው አህአዴግ ከመላው የአገራችን ህዝብ ጋር በመሆን አምባገነን የሆነውን የደርግ ስርዓት በገረሰሰ ማግስት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በደረግ ዘመነ መንግስትም ሆነ ከዛ በፊት ባሉ የስልጣን ዘመናት በአገራችን የሃሳብ ልዩነትን የሚያስተናግድ አስቻይ ሁኔታ ፈፅሞ እንዳልነበረ ይታወሳል፡፡ ነገስታቱም ሆነ ደርግ ስልጣንን ለህዝብ ማገልገያ መሳሪያነት ሳይሆን የማይነካ የተጠበቀ ቦታ አድርገው በመውሰዳቸው የሃስብ ልዩነት ያላቸውን ስብስቦች ለመቀበል እንኳንስ የህግ ይቅርና የሞራል ዝግጅትም አልነበራቸውም፡፡

አሁን በአገራችን እያጣጣምነው ስላለው ዴሞክራሲና የመድብለ ፓርቲ ስርዓት ሁኔታ ስናወራ እያወራን ያለነው የ25 ዓመታት እድሜ ልምድን መሆኑን መገንዘቡ አይከፋም፡፡ በእኔ እምነት ዴሞክራሲ በህብረሰተብ ውስጥ እየተገነባ የሚሄድ የአስተሳሰብ ስልጥንና ነው፡፡ የመናገር የመጻፍና የመቃወም መብቱ ለዘመናት ተነፍጎ ለቆየ የህብረተሰብ ክፍል ስለ ዴሞክራሲ አጠቃላይ ሁኔታ ያለውን ግንዛቤ ይዞት ከመጣው አስተሳሰብ ጋር ለማዛመድ ጊዜ የሚወስድበት ከመሆኑ ባሻገር ምናልባትም ዴሞክራሲ የሚለው ሃሰብ በራሱ የተገለለና አላስፈላጊ አድረጎ መቁጠሩም ሆነ በአግባቡ መጠቀም ላይ በሁሉም የህብረተሰባችን ክፍል መኖሩ የማይቀር ነው፡፡ በአገራችን የ25 ዓመታት ጉዞ ውስጥ ዴሞክራሲያችን ከተነሳበት አንፃር እየጎለበተ ይምጣ እንጂ አሁንም በብዙ ተግዳሮቶች የተሞላ መሆኑን ማስመር ያስፈልጋል፡፡

ስለዴሞክራሲ ስናወራ ምርጫ ቦርድን ጨምሮ ሌሎች ዴሞክራሲያዊ ተቋማትን ማንሳታችን አይቀርም፣ ስለዴሞክራሲ ስናወራ የህዝብ ተሳትፎን እናወራለን፣ ስለዴሞክራሲ ስናወራ ስለ መንግስት ስልጣንና የስልጣን ክፍፍል እናነሳለን፣ ስለዴሞክራሲ ስናነሳ ተያይዘው የሚነሱ በርካታ ጉዳዮች አሉ፡፡ ይህ የሚያመላክተው ዴሞክራሲንና ዴሞክራሲያዊ መብቶችን የመጠቀም ጉዳይ ሰፊና የራሱን ጊዜ የሚፈልግ መሆኑን የሚያረጋግጥ ነው፡፡ በአገራችን የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ እውን ከሆነበትና ስልጣን በዜጎች መልካም ፍቃድ ላይ በተመሰረተ ነፃ ምርጫ መወሰን ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ዜጎች ዴሞክራሲያዊ መብቶቻቸውን የመጠቀም ልምዳቸው ከመጎልበቱ ባሻገር የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታችንም እየዳበረ መምጣት ችሏል፡፡

የመድብለ ፓርቲ ስርዓት በአገራችን እውን መሆኑ በአገራችን የህዝብን ስልጣን መምራት የሚችለው በህዝብ የተመረጠ ፓርቲ መሆኑን ከመስረገጡ ባሻገር ዜጎች መብቶቻችንን ያስከብሩልናል ብለው ባሰቧቸው ድርጅቶች ላይ ራሳቸውን በማስገባት መብቶቻቸውን የሚጠቀሙበት እድል ሰፊ እንዲሆን አስችሏል፡፡ በዚህም ባለፉት ዓመታት ለመድበለ ፓርቲ ዴሞክራሲው መፋፋት የራሳቸውን ድርሻ መወጣት የሚችሉ በርካታ የፖለቲካ ፓርቲዎች ተመዝግበው ፍላጎታቸውን በማንፀባረቅ ላይ ይገኛሉ፡፡

በያዝነው ሳምንት የህዝብ ስልጣን እየመራ ያለው ኢህአዴግ እና 20 የሚሆኑ ህጋዊ በሆነ መንገድ ተመዝግበው በአገር ውስጥ እንቅስቃሴ እያደረጉ ያሉ ተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች በአገራቸው ጉዳይ ላይ ውይይትና ድርድር ለማካሄድ የሚያስችላቸውን ስምምነት አድርገዋል፡፡
ኢህአዴግና ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ ባካሄዱት ውይይት በሚያስማሙ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት ለማካሄድና ድርድርና ክርክር በሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ ደግሞ እንደአስፈላጊነቱ ድርድር ወይም ክርክር ለማካሄድ የሚያስችላቸው ቅደመ ሁኔታ ማዘጋጀት ላይ ተወያይተዋል፡፡ በዚህም በቀጣይ ከሚካሄዱ የጋራ መድረኮች በፊት በስብሰባ ስናስርዓት፣ በአጠቃላይ የመድረክ ሁኔታና በታዛቢ መረጣ ዙሪያ ሊኖሩ የሚገቡ ቅድመ ሁኔታዎችን አማራጮችን በጽሑፍ እስከ ጥር 25 ቀን 2009 . ድረስ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት /ቤት ለማስገባት ተግባብተዋል፡፡

በውይይቱ በአብዛኛው የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ይህ ውይይት መጀመሩንና የቀጣይ ድርድሮችንም ሆነ ክርክሮችን ለማድረግ በሚያስችሉ ቅድመ ሁኔታዎች ላይ ለመነጋገር ኢህአዴግ ኃላፊነቱን ወስዶ መሰብሰቡ የሚመሰገን መሆኑን የገለፁ ሲሆን ፓርቲዎቹ ቀጣይነቱ ላይ ያላቸውን ስጋት ኢህአዴግ ምን ያህል ቁርጠኛ ነው የሚል ሃሳብ በመሰንዘር ገልጸዋል፡፡
ኢህአዴግ በአገራችን የመድብለ ፓርቲ ዴሞክራሲ እንዲጎለብት በአገር ውስጥ ካሉ ህጋዊ  የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ተቀራርቦ ለመስራት ያለውን ፍላጎትና ቁርጠኝነት በተደጋጋሚ ገልጿል፡፡ ኢህአዴግ በአገራችን ያሉ ህጋዊ ተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች እንደየራሳቸው ነባራዊ ሁኔታ የሚደግፏቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ያሉ በመሆነቸው እነዛ የህብረተሰብ ክፍሎች ድምፃቸው የሚሰማበት ሁኔታ መኖር እንዳለበት ያምናል፡፡ በመሆኑን የምርጫ ህጉን ከማሻሻል ጀምሮ ሌሎች ርምጃዎችንም ለመውሰድ ያለውን ቁርጠኝነት አሳይቷል፡፡ በመሆኑም ኢህአዴግ በተለያዩ ድርጅታዊ ስብሰባዎችና መግለጫዎች እንዳሳወቀው ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የሚያደርገውን ተቀራርቦ የመስራት ቁርጠኝነት አጠናክሮ የሚቀጥልበት መሆኑን ከህዝባዊ ባህሪው በመነሳት መደምደም ይቻላል፡፡
በውይይቱ እንደተመላከተውም ኢህአዴግ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች በተጨማሪ ከምሁራንና ከሲቪክ ማህበራት ጋር ውይይት እንደሚያካሄድ በማስታወቅ ሁሌም ቢሆን ልምዶቻችንን በመቀመርና በቀጣይ መስተካከል የሚገባቸው ሁኔታዎች ላይ በመወያየት በአገራችን የዴሞክራሲ ስርዓት ግንባታችን እንዲያብብ እንደሚሰራ ውይይቱን ሲመሩ የነበሩት አቶ ሽፈራው ሽጉጤ አስረግጠው ገልጸዋል፡፡

ውድ አንባብያን በእኔ እምነት ያለውን የሰጠ ንፉግ አይባልም ነውና ተረቱ ኢህአዴግ ከተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር አብሮ ለመስራት ያለውን ቁርጠኝነት በተደጋጋሚ መግለፁ ይበል የሚያሰኝ ነውና ተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲዎች አብረው መስራታቸውና መታረም ያለባቸውን በማረም መጎልበት ያለባቸውን ደግሞ እንዲጎለብቱ በማድረግ ሁሉም ለአገራቸው የሚበጀውን ማድረጋቸው ዞሮ ዞሮ ጥቅሙ ህዝብ ላይ የሚያርፍ ነውና መጠራጠሩን ወደ ጎን በመተው በተጨባጭ ጉዳዮች ላይ በርትቶ መስራት ይጠበቃል፡፡


የኢፌዴሪ ፕሬዝዳንት ዶክተር ሙላቱ ተሾመ 2009 . የመንግስትን የትኩረት አቅጣጫዎች ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና ለፌዴሬሽን ም/ቤት የጋራ የመክፈቻ ስነስርዓት ባቀረቡበት ወቅት በአገሪቱ ውስጥ በህጋዊና ሰላማዊ መንገድ ከሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የተለያዩ የውይይት መድረኮች እንደሚካሄዱ መግለጻቸው ይታወሳል። ይህን ተከትሎም በጠቅላይ ሚንስትር ጽሕፈት ቤት ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር የሚደረጉ ውይይቶች የሚከታተል ማዕከል ተቋቁሟል። መሪ ድርጅቱ ኢህአዴግም ከሰላማዊና ሕጋዊ የፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር ውይይቶች ለማድረግ መዘጋጀቱን አስታውቋል። ይህ የኢህአዴግን ቁርጠኝነት የሚያረጋግጥ በመሆኑ ሁሉም ፖለቲካ ፓርቲዎች የነገዋን ሰላማዊና ዴሞክራያዊ ኢትዮጵያ ለመገንባት የጋራ ርብርብ የሚጠይቅ የለውጥ እንቅስቃሴ ውስጥ በመግባት የድርሻቸውን ለመወጣት መትጋት ይገባቸዋል፡፡ በእኔ እይታ ይህ የተጀመረው እንቅስቃሴ ግን በራሱ ግብ ባይሆንም ይበል የሚያሰኝ ነውና ሳይደናቀፍ እንዲቀጥል ሁሉም ፓርቲዎች በቁርጠኝነት ሊሰሩ ይገባል ባይ ነኝ፡፡ ሰላም፡፡ 

No comments:

Post a Comment