EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Wednesday 11 January 2017

የፀረ ኪራይ ሰብሳቢነት ትግሉ የሕዝቡን ንቁ ተሳትፎ ግድ ይላል

(በውብዓለም ፋንታዬ)
የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ በአንድ ወቅት የሚጠናቀቅ ሳይሆን በሂደት የሚከናወን ነው፡፡ የስርዓት ግንባታውን ከዳር ለማድረስ በሂደቱ ከውስጥና ከውጭ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶችን ማለፍ ያስፈልጋል፡፡ በሀገራችን እየተካሄደ የሚገኘው የልማታዊ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ በእስከአሁኑ ሂደት ውጣ ውረዶች ሳይበግሩት በርካታ ድሎችን አስመዝግቧል፡፡ በሂደቱ ያጋጠሙ በርካታ ተግዳሮቶችን ታግሎ በማስተካከል ሂደቱን ለማሳለጥ ተሞክሯል፡፡
  
የስርዓት ግንባታውን እየተፈታተኑት ከሚገኙ ችግሮች ውስጥ አንዱ የሆነው የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትና ተግባር ሲሆን በዚህ ላይ ትግል ከተጀመረ ሰነባብቷል፡፡ ይህ በመሆኑም ባለፉት 15 ዓመታት ከየትኛውም መሰል ሀገር የተሻለ እድገት ማስመዝገብ ችለናል፡፡ በየሴክተሩ በተደረገው ርብርብ መጥፎ ገጽታችን በለውጥ ተምሳሌትነት ተቀይሯል፡፡ ሆኖም ግን አሁንም ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ ስርዓታችን ከኪራይ ሰብሳቢነት ችግር ባለመላቀቁ ትግሉ ሊቀጥል ግድ ነው። 
ኪራይ ሰብሰቢነት ከገበያ ውድድር ውጪ ለስልጣን ባለ ቀረቤታ አማካኝነት ያልተገባ ጥቅም የሚግበሰብስበት የዜሮ ድምር ስልት ነው፡፡ ይህ ተግባርና አመለካከት ለኢኮኖሚው ባበረከቱት አስተዋጾ ልክ ከሚገኝ ፍትሃዊ ጥቅም ጋር ፍጹም ተቃራኒ የሆነ አካሄድ ሲሆን፤ ስር እየሰደደ በሄደ ቁጥር በሀገር ውስጥ የሚገኘው ኃብት በጥቂቶች ቁጥጥር ስር እንዲውል መንገድ የሚከፍትና ብዙኃኑን የሚያገልል ሁኔታ እንዲፈጠር የሚያደርግ ነው፡፡
በተከታታይ አመታት በግብርና ገጠር ልማት ዘርፍ ባደረግነው ርብርብና በተመዘገበው ስኬት የተነሳ መላው አርሶ አደራችን የብልፅግናው ምንጭ የራሱንና የቤተሰቡን ጉልበት አስተባብሮ በማሳው ላይ የሚያደርገው ጥረት ብቻ መሆኑን መረዳት ከጀመረ ውሎ አድሯል። በዚህ የተነሳ በገጠር የኪራይ ሰብሳቢነት ፖለቲካ ኢኮኖሚ እየተደፈቀ በምትኩ ልማታዊነት እያደገና የበላይነቱን እየያዘ መጥቷል። በከተሞች ግን የኪራይ ሰብሳቢነት ምንጮች እንደሆኑ በሚታወቁት የመሬት አስተዳደር፣ ግብር እና ታክስ፣ የመንግስት ግዢ ጋር በተያያዘ አሁንም የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትና ተግባር የዴሞክርሲያዊ ስርዓት ግንባታችን ዋነኛ ፈተና ሆኖ ይገኛል። በተለይ በድርጅታችንና በመንግስት ውስጥ ከታየው ስልጣንን ለህብረተሰብ ለውጥ ሳይሆን ለግል ኑሮ ማበልፀጊያነት የመጠቀም አዝማሚያና ተግባር ጋር ተያይዞ ኪራይ ሰብሳቢነት በከተሞች እየገነገነ፣ በገጠር ደግሞ እያንሰራራ መምጣት ጀምሯል።
በስልጣን ላይ በሚገኙ ጥቂት ግለሰቦችና በነዚህ አካባቢ በተኮለኮሉ ተባባሪዎቻቸው አማካይነት የሚፈጸመው ኪራይ ሰብሰቢነት ካለው ውስብስብ ባህሪ የተነሳ እያደር እያቆጠቆጠና አድማሱን እያሰፋ መጥቷል ማለት ይቻላል፡፡ ባለፉት ወራትም ሰላማችንን እስከ ማናጋት ደረጃ መድረሱን ተመልክተናል፡፡ ለዚህ ተግባርና አመለካከት መቋጫ ካልተበጀለት የጀመርነው ልማትና እንደሀገር የሰነቅነውን ራዕይ ለማሳካት አዳጋች ሊሆን እንደሚችል አመላካች ነው፡፡
ኪራይ ሰብሰቢነት የህዝብን ጥቅም ከሚያስቀድመው ከኢህአዴግ መሰረታዊ መርህ ጋር በእጅጉ የሚጣረስ በመሆኑ ኢህአዴግ ችግሩን ከነምንጩ ገምግሞ ይህንን ለመቀልበስ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ በየደረጃው በተዘረጉ የጥልቅ ተሃድሶ መድረኮች አማካኝት የተለያዩ እርምጃዎችም እየተወሰዱ  ይገኛሉ፡፡ በእስካሁኑ ሂደት የአሰራር ግልጽነትና ተጠያቂነትን በማስፈን የህዝብን ፍላጎት ለማርካት እንዲቻል በፌዴራልም ሆነ በክልሎች ብቃትና የህዝብ ውግንናን መሰረት ባደረገ መልኩ አስፈጻሚውን አካል መልሶ የማደራጀት ስራዎች ተከናውነዋል፤ በከተሞችና በወረዳዎችም በተመሳሳይ እየተተገበረ ይገኛል፡፡ በተጨማሪም በድርጅትም ሆነ በመንግስት መዋቅር ውስጥ አጥፊዎችን የመለየት ስራዎች እየተከናወኑ ነው፡፡
ይህም ሆኖ ግን በኪራይ ሰብሳቢነት ላይ የተጀመረው ትግል መሪው ድርጅት ኢህአዴግና የኢፌዴሪ መንግስት በሚያደርጉት ጥረት ብቻ ሊሳካ አይችልም፡፡ ይህንን ትግል ከዳር ለማድረስና ችግሩን ለመቅረፍ የሁሉንም ባለድርሻ አካላት በተለይም የሰፊውን ሕዝብ ያልተቆጠበ ርብርብ የሚጠይቅ ነው፡፡ ለተሃድሶው ውጤታማነት በተለይም የችግሩ ዋነኛ ተጎጂ የሆነው የህዝቡ ተሳትፎ ያለው ሚና  ከፍተኛ  በመሆኑ በየደረጃው በተዘረጉ የተሃድሶ መድረኮች በመሳተፍ እያንዳንዱ የህብረተሰብ ክፍል የሚጠበቅበትን ሊወጣ ይገባል፡፡ በድርጊቱ የተሳተፉትን፣ ጥቅሙንና መብቱን የተጋፉትን፣ በአገልግሎት አሰጣጥ እንዲማረር ያደረጉትን ኃላፊዎችና ፈጻሚዎችን በመታገልና በማጋለጥ ከስህተታቸው እንዲማሩ፣ በደረቅ ወንጀል የተሳተፉ ደግሞ ለህግ እንዲቀርቡ አስፈላጊውን እገዛ ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡  

የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደሳለኝ እንደተናገሩት “ችግሮችን ከምንጩ ለማድረቅ የህዝብ ተሳትፎ ወሳኝ ነው፡፡ ለአብነትም ጉቦ ካለ ጉቦ ሰጪና ተቀባይ አለ፡፡ ችግሩን ለመፍታት ጉቦ ሰጪው “ጉቦ አልሰጥም” ብሎ መወሰን አለበት፡፡ ህዝቡ ጉቦ አልሰጥም ብሎ ካመረረ ጉቦ ተቀባዩ ምንም ሊሆን አይችልም፤ ተስተካክሎ ይሄዳል፡፡ የመንግስትና ህዝብ አንድ ላይ ሆኖ መስራት መሰል ችግሮች እንዲስተካከሉ ያደርጋል፡፡ በመንግስት በኩል ችግሩን ለመቅረፍ ቁርጠኝነቱ አለ፡፡ የህዝብ ቀጥተኛ ተሳትፎ ከታከለበት የማይሳካበት ምክንያት የለም፡፡” ስለሆነም ሲሾም ያልበላ፤ ሲሻር ይቆጨዋል›› የሚሉና ያልተገባ ጥቅም ማግኘትና በአቋራጭ የመክበር ፍትሃዊነትን ከሚሰብኩ አስተሳሰቦች ራሱን ከማራቅ ጀምሮ ህብረተሰቡ በምንም መልኩ መብቱን በገንዘብ ላለመግዛት፣ በመብቱ ከአመራሩም ሆነ ከፈጻሚው አካል ጋር በህገ ወጥ መንገድ ላለመደራደር ቁርጠኛ አቋም መያዝና ተግባሩን ሊጸየፍ ይገባል፡፡

No comments:

Post a Comment