EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Wednesday 28 September 2016

የዘንድሮው የትምህርት ማህበረሰብ ውይይት ባለ ድርብ ፋይዳ ነው!!


(በክሩቤል መርሃጽድቅ)
በኢህአዴግ የሚመራው ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስት በሁሉም የሀገራችን አካባቢዎች በትምህርት መስክ አንጸባራቂ ድሎችን ተጎናጽፏል፡፡ ይህ ድል ኢህአዴግ  ትምህርት ለሁለንተናዊ ልማት ያለውን ከፍተኛ ፋይዳ በመገንዘብ ለመስኩ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ በመስራቱ የተገኘ ውጤት ነው፡፡ የትምህርት ተደራሽነትን ለማረጋገጥ በተያዘው ሀገራዊ ግብ መሰረት በሁሉም አካባቢዎች ከቅድመ መደበኛ እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ማስፋፋት ተችሏል፡፡ ቀደም ባሉት ስርዓቶች በከተሞች ብቻ ተወስነው የነበሩ ትምህርት ቤቶች ኢህአዴግ በወሰደው ቆራጥ ውሳኔ ለሁሉም የገጠር ቀበሌዎች ተዳርሰዋል፡፡

በያዝነው ዓመትም ወደ 30 ሚሊዮን የሚጠጉ ዜጎች በትምህርት ገበታ ላይ ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡ ይህ ቁጥር ከአጠቃላይ የኢትዮጵያ ህዝብ ሲሰላ ከሩብ በላይ ነው፡፡ እነዚህ በትምህርት ገበታ ላይ የሚገኙ ህጻናትና ወጣቶች የነገይቱን ኢትዮጵያ ዕጣ ፈንታ በመወሰን ረገድ ቁልፍ ሚና መጫወታቸው አይቀርም፡፡ ተገቢውን ዕውቀትና ክህሎት ጨብጠው፣ በስነ ምግባር ታንጸው እንዲሁም ዴሞክራሲያዊ ባህሪ ተላብሰው ከወጡ የተጀመረውን የልማት፣ የሰላምና የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ሂደት ወደ ፊት በማራመድ የህዳሴ ጉዟችንን እውን ለማድረግ የማይተካ ሚና የሚጫወቱ ይሆናሉ፡፡
በጥቂት ዓመታት ውስጥ ኢትዮጵያን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለማሰለፍ ብሎም የኢትዮጵያን ህዳሴ ለማረጋገጥ እየተጋ ያለው ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስታችን በሀገሩ ሁለንተናዊ ልማት የበኩሉን ድርሻ የሚወጣ ብቁ የሰው ኃይል ለማፍራት ከፍተኛ ርብርብ እያደረገ ይገኛል፡፡ በትምህርት ተደራሽነት የተመዘገበውን ስኬት በጥራትም ለመድገም የትምህርት ጥራት ፓኬጅን ቀርጾ ተግባራዊ በማድረግ ላይ ያለውም ይህንን ሀገራዊ ተልእኮ በአግባቡ ለማሳካት ነው፡፡
በትምህርት መስክ የተያዘው ራዕይ ይሳካ ዘንድ መንግስት የመስኩ ባለቤቶች ከሆኑት የትምህርት ተቋማት ሰራተኞች፣ መምህራንና ተማሪዎች ጋር ተቀራርቦ መስራት እንዳለበት ተገንዝቦ በየጊዜው የተለያዩ መድረኮችን እየፈጠረ በቀጣይነት እየተመካከረ ይገኛል፡፡ ከ2006ዓ.ም ጀምሮ በክረምት ወራት ለትምህርት ተቋማት የባለድርሻ አካላት የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮች እየፈጠረም ከምንጊዜውም በላይ ተቀራርቦ ለመስራት ጥረት በማድረግ ላይ ነው፡፡ መድረኮቹ በትምህርት ተቋማት የሚታዩ ችግሮች ግልጽ ሆነው እንዲወጡ የሚያደርግ በመሆኑ የሚመለከተው አካል ችግሮቹን በቀጣይነት ለመፍታት የሚያስችል ሰፊ ዕድል ይፈጥራል፡፡ የመማር ማስተማር ሂደትን የሚያውኩ የዲስፕሊንና የአመለካከት ችግሮችን ለመፍታትም አይነተኛ ድርሻ ይኖራቸዋል፡፡ ቀደም ባሉ ዓመታት በተሰጡ ስልጠናዎች የተገኘው ተሞክሮም ይህንን እውነታ ያረጋግጣል፡፡ ስልጠናዎቹ በተለይም የትምህርት ተቋማት የመልካም አስተዳደር ችግሮችን በመፍታት ረገድ ከፍተኛ ሚና በመጫወት ላይ ናቸው፡፡
በዚህ አመት ከመምህራንና ከአስተዳደር ሰራተኞች ጋር የተካሄደው ውይይትም ቀደም ሲል እንደተካሄዱ ውይይቶች ሁሉ የየተቋማቱን ሰላማዊ የመማር ማስተማር ሂደት ውጤታማ በማድረግ ረገድ የጎላ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ይታመናል፡፡ የዘንድሮዎቹ መድረኮች የእስካሁን ልምዶችን በመጠቀም ለበለጠ ውጤታማነት መስራት የሚያስችሉ ናቸው፡፡ ከዚህ በፊት ከተሰጡ ስልጠናዎች የተገኙ ልምዶችን ይበልጥ ለማስፋትና በሂደቱ በመንግስትም በተቋማቱም ደረጃ ያጋጠሙ ጉድለቶችንም ለማረም እንደሚያስችሉ ይታመናል፡፡

መድረኮቹ የተካሄዱበት ወቅት ድርጅታችን ዳግም በጥልቀት ለመታደስ ንቅናቄ ማድረግ የጀመረበት መሆኑ ደግሞ መድረኮቹ ለተሃድሷችን ግብዓት ሆኖ የማገልገል ድርብ ፋይዳ እንዲኖራቸው ያደርጋል፡፡ ከመምህራንና ሰራተኞች ጋር የተካሄደው ውይይት በቀጣይ ከወላጆችና ተማሪዎችም ጋር ከሚካሄዱ ውይይቶችና ከመላው ህዝባችን ጋር ከሚካሄዱ ውይይቶች ጋር ተዳምሮ ተሃድሷችን ይበልጥ ጥልቀትና ስፋት እንዲኖረው የሚያስችል ይሆናል፡፡

No comments:

Post a Comment