EPRDF is a ruling party committed to realize Ethiopia's Renaissance.

Wednesday 3 August 2016

የጋራ ቤታችንን በጋራ እንገንባ!!

(በኤፊ ሰውነት)
በባህር ዳር ከተማ ከሐምሌ ­25 ቀን 2008ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ቀናት ሲከበር የቆየው የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ቀን ፍፃሜውን አግኝቷል፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃ የዲያስፖራ ቀን ሲከበር ይህ ለሁለተኛ ጊዜ ሲሆን የዚህ በዓል መከበር ዋነኛ ዓላማም በአገራችን የተጀመረውን ልማት ለማስቀጠልና የአገራችንን ህዳሴ ለማረጋገጥ በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች የሚገኙት ዜጎቻችን የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ ለማስቻልና በዚህም የጋራ መግባባት ለመፍጠር ነው፡፡ የበዓሉ መሪ ቃልም የሚያስረግጠው ይህንኑ ነው -“የኢትዮጵያ ህዳሴ በሀገር ልጆች”፡፡
ይህ የዲያስፖራ ቀን እንደ በዓል መከበሩ በተለያዩ የዓለማችን ክፍል የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን የአገራቸውን የልማት ጥሪ ተቀብለው ከያሉበት በመሰባሰብ አገራቸው ያለችበትን ነባራዊ ሁኔታ የተመለከተ ትክክለኛ ምስል ከመረዳት ባሻገር አገራዊ ህልማችንን ለማሳካት በምናደርገው ሁሉን አቀፍ ርብርብ የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ የሚያስችልና የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው የሚያግዝ መሆኑ አያጠያይቅም፡፡
የአገራችን ህዳሴ ሊፋጠን ከሆነ ዲያስፖራው ከመቼውም ጊዜ በላቀ ሁኔታ ድህነትን ድል ማድረግ ህልሙ አድርጎ እየሰሩ ካሉት የኢትዮጵያ ህዝቦችና ልማትን የሞት የሽረት ጉዳይ አድርጎ ከያዘው ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስታችን ጎን በመሰለፍ የጋራ ርብርብ ማድረግ የግድ ይላቸዋል፡፡
በአገራችን ከ1983ዓ.ም በፊት የነበሩ ህጎችና መመሪያዎች እንኳንስ በውጭ ለሚኖረው ዲያስፖራ ይቅርና በአገሩ እየኖረ ሃብቱን ማፍሰስ ለሚፈልገው ባለሃብት የሃብት ገድብ የሚጥሉና የማያሰሩ ቀፍዳጅ ፖሊሲዎች እንደነበሩት ይታወቃል፡፡ ይህም በአገራችን የነበረው የዲያስፖራ ተሳትፎ ከቁጥር የማይገባ እንዲሆን አድርጎት ነበር፡፡ በተለያዩ የዓለማችን ክፍል የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንም በአገራቸው የልማት ሂደት ወስጥ የውጭ ተመልካች ከመሆን ያለፈ ተግባራዊ እንቅስቃሴ ሳያደርጉ ዓመታትን ለማሳለፍ ተገደዋል፡፡ ሁሉም ዜጋ እንደየአቅሙ ያልተሳተፈበት ልማት ደግሞ ውጤቱ ዞሮ ዞሮ ተንገራግጮ መቆም ነውና ሀገራችንም የድህነትና የኋላቀርነት ተምሳሌት ለመሆን በቅታ ነበር፡፡ የተወሰነውን የሕብረተሰብ ክፍል ያገለለ የልማት ጉዞ በአንድ እጅ እንደ ማጨብጨብ አይደል ነገሩ፡፡
በኢህአዴግ የሚመራው ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስታችን ግን ባለፉት ዓመታት ሁሉም ዜጋ በአገሩ ጉዳይ ላይ በያገባኛል መንፈስ ሲያከናውናቸው የቆዩት ተግባራት ያለፉ ዘመናት ጨለምተኛ ታሪካችንን በመለወጥ ብሩህ የህዳሴ ጭላንጭል አሳይቶናል፡፡ ኢህአዴግ አገር የማስተዳደርና ህልውናችንን የማስቀጠል ህዝባዊ ኃላፊነት ከተረከበበት ጊዜ አንስቶ አገራችን እያንዳንዱ ዜጋ በሚያደርገው ተሳትፎ ልክ እድገቷ የሚፋጠንና የሁላችንንም ርብርብ የምትፈልግ መሆኗን በመረዳት የእያንዳንዱን ዜጋ ተሳትፎና ተጠቃሚነት የሚያረጋግጡ የተለያዩ የልማት፣ የሰላምና የዴሞክራሲዊ ስርዓት ግንባታ ፖሊሲዎች፣ ስትራቴጂዎችና ከእነዚህ የሚቀዱ መመሪያና አሰራሮች እንዲቀረፁ አድርጓል፡፡ በተለያዩ የዓለማችን ክፍል የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና ትውልድ ኢትዮጵያውያንም በአገራቸው ያለውን ምቹ የልማት፣ የሰላምና የዴሞክራሲ ሁኔታ ከግምት ውስጥ በማስገባት እንደባለፉት ስርዓታት ከአገራቸው የሚሸሹ ሳይሆኑ ፊታቸውን ወደ አገራቸው እንዲያዞሩ የሚያስችል ሰፊ ዕድል አግኝተዋል፡፡
ዲያስፖራዎች ለዘመናት ያጠራቀሙት ሃብት፣ እውቀትና ልምድ የአገራችንን መጥፎ ገፅታ በመቀየር፣ በአቅማቸው በሚያደርጉት ተሳትፎ እድገቷን በማፋጠንና ከድህነት ጋር የጀመርነውን ትግል ድል በመንሳት በኩል ጉልህ ሚና መጫወት እንደሚችል እሙን ነው። የኢትዮጵያ መንግስትም ይህን ለማሳካት የሚያስችሉ ተግባራትን እየፈፀመ ይገኛል፡፡ እነዚህ የልማት አቅሞች በአገራቸው ሁለንተናዊ እድገት ላይ የበኩላቸውን ድርሻ እንዳይወጡ የሚያደርጋቸውን አሰራር በመፈተሽና በመመካከር ያለውን ምቹ ሁኔታም ለዲያስፖራዎቹ በማሳወቅ ረገድ ዘርፈ ብዙ ጥረት እየተደረገ ነው፡፡ መንግስት በኢትዮጵያውያንና በትውልደ ኢትዮጵያውያን የሚካሄደውን ኢንቨስትመንት ለማሳለጥ ከውጭ ባላሃብቶች በተለየ ሁኔታ ማበረታቻዎችን በመስጠት ቁርጠኝነቱን በተጨባጭ ማሳየት ችሏል፡፡ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የፀደቁ መመሪያዎችና የዲያስፖራ ፖሊሲ የመንግስት ቁርጠኝነት ተጨባጭ ማሳያዎች ተደርገው የሚወሰዱ ናቸው፡፡
በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያንና ትውልድ ኢትዮጵያውያን በአገራቸው መዋዕለ ነዋያቸውን ለማፍሰስ የሚያስችላቸውን ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር አኳያ ለእነሱ ብቻ የተፈቀዱ ማበረታቻዎች መተግበር ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ የታክስ እፎይታ ጊዜ መስጠት አንዱ ነው። አንድ ኢትዮጵያዊ ባለሃብት በማምረቻ ኢንዱስትሪ፣ በግብርና ውጤቶች ማቀነባበር አልያም በቀጥታ በግብርና ምርት ላይ የተሰማራ እንደሆነና ከ50 በመቶ በላይ ምርቱንና አገልግሎቱን ወደ ውጭ የሚልክ ከሆነ፣ ወይም ከ75 በመቶ በላይ የሚሆነውን ምርቱን በወጭ ንግድ ለተሰማራ አካል የሚያቀርብ ከሆነ ለአምስት ዓመት የሚቆይ የታክስ እፎይታ ጊዜ እንደሚሰጠው ተደንግጓል፡፡ የታክስ እፎይታ ጊዜን በተመለከተም ይህንና መሰል ዝርዝር መመሪያዎችን በማውጣት ለማበረታታት ጥረት ተደርጓል፤፡፡ የእፎይታ ጊዜው ባለሃብቱ ምርትና አገልግሎቱን ማቅረብ ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ እንዲሆን መደረጉም እንዲሁ፡፡ ይህ ባለሃብቱ በእግሩ እስኪረግጥ ድረስ በተደማሪ ጉዳዮች ላይ እንዳይወጠር ከማድረግ አኳያ የላቀ ፋይዳ ያለው ፖለቲካዊ ውሳኔ ነው።
ከዚህ ባሻገርም በአገራችን ያሉ እምቅ ተፈጥሯዊ ሃብቶቻችንን ከማሳወቅና ክልሎችም ይህን የዲያስፖራ ፍላጎት ማሟላት በሚችሉበት ቁመና ላይ እንዲሆኑ የጋራ አቋም ከመያዝ ጀምሮ በፌዴራልና በክልል ደረጃ ዲያስፖራውን የሚያግዙና ጉዳዩን የሚከታተሉ መዋቅሮችን መዘርጋት ችሏል፡፡ ከዚህ ባሻገር የዲያስፖራ አካላትን ተሳትፎ ለማበረታታት ለትወልድ ኢትዮጵያውያን የዜግነት መለያ ካርድ (Yellow Card) በመስጠት የዲያስፖራውን ስጋቶች ማስወገድና እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ አገልግሎቶችን በቀላሉ መጠቀም የሚያስችላቸውን ሁኔታ መፍጠር ተችሏል፡፡ ይህ በተለይ በትውልድ ኢትዮጵያዊ ሆነው የሌላ አገር ዜግነት ላላቸው ኢትዮጵያውያን እንደ ኢትዮጵያዊ ዜጋ እኩል መብት እንዲኖር ያስቻለ በመሆኑ ለዲያስፖራው ትልቅ እርምጃ ተደርጎ የሚወሰድ ነው፡፡
ወደ አገር ውስጥ የሚገቡ መገልገያዎችን ከቀረጥ ነፃ ማድረግ፣ ዲያስፖራው ተሽከርካሪዎችን፣ የግንባታ እቃዎችንና መሰል መሳሪያዎችን ከታክስ ነፃ በሆነ መልኩ እንዲያስገቡ የሚያስችል ስርዓት ተዘርግቶ ተግባራዊ ሆኗል፡፡ በኢትዮጵያ የሚኖሩም ሆነ ከኢትዮጵያ ውጭ የሚኖሩ ኢትዮጰያውያን በውጭ ምንዛሬ በኢትዮጵያ የማጠራቀሚያ የባንክ ሒሳብ እንዲኖራቸው ፍቃድ አግኝተዋል፡፡ ይህም ዲያስፖራው በረጅም ጊዜ በሚያጠራቅምው ገንዘብ በአገሩ መዋእለ ንዋዩን እንዲያፈስ ለማድረግም ይሁን ለመገበያየት አለያም የብድር አገልግሎት ለመጠቀም መልካም አማራጭ በመሆኑ ለዲያስፖራው ታስቦ የተዘረጋ አሰራር ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር የአገር ወሰጥ ባለሃብቱን የካፒታል፣ የእውቀትና የልምድ ችግር ለመቅረፍና የቴክኖሎጂ ሽግግር ለማሳለጥ እንዲቻል የአገር ውስጥ ባለሃብቱ ከውጭ ባለሃብት ጋር በጣምራ ኢንቨስትመንት እንዲሰማራ የሚያስችለውን ሁኔታም ማመቻቸት ተችሏል፡፡ 
እነዚህ ከላይ የተዘረዘሩ የፖሊሲ እርምጃዎች የሚያረጋግጡት ጉዳይ ልማታዊና ዴሞክራሲያዊ መንግስታችን በውስጥም በውጭም ያለው ኢትዮጵያዊና ትውልደ ኢትዮጵያዊ በቀጥታ የልማታችን ተሳታፊና ተጠቃሚ እንዲሆን ለማስቻል የተቀየሱ መሆናቸውን ነው፡፡ ታላቁ መሪ መለስ ዜናዊ በአንድ ወቅት ከዲያስፖራዎች ጋር ባደረጉት ውይይት እንደገለፁት እኛ አንድ አገርና ፓስፖርት ነው ያለን፤ ወደድንም ጠላንም ኢትዮጵያዊ ነን፡፡ ኢትዮጵያዊ ደግሞ እንደ ኢትዮጵያዊነቱ በአገሩ ጉዳይ ላይ ይመለከተኛል በሚል መንፈስ ነው መስራት የሚገባው፡፡ ማንም ኢትዮጵያዊው በአገሩ ጉዳይ ላይ የሩቅ ተመልካች ሳይሆን በልማቱ፣ በሰላሙና በዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታው በቀጥታ የመሳተፍ የዜግነት ግዴታም ጭምር አለበት፡፡
አሁንም ገና ብዙ ስራ የሚጠይቅና ብዙ እርምጃ ወደፊት መጓዝ እንዳለብን ግልፅ ቢሆንም ባለፉት ዓመታት ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ያጠራቀሙትን ሃብትና እውቀት በአገራቸው ላይ ማፍሰስ ጀምረዋል፡፡ እስካሁን በተከናወኑ በርካታ የልማት፣ የሰላምና የዴሞክራሲያዊ ስርዓት ግንባታ ስራዎች አማካይነትም ዛሬ አገራችን በእድገት ጎዳና ላይ ወደፊት እየገሰገሰች ትገኛለች። ይህ ለዓመታት በመንግስታችንና በህዝባችን ሁሉን አቀፍ ርብርብ አማካይነት የተረጋገጠ ውጤት ሲሆን ስራው በቀጣይነትም ተጠናክሮ መቀጠል ያለበት ነው፡፡ የዲያስፖራ ቀን የመከበሩ ዋና ዓላማም በዚህ ማዕቀፍ የሚታይ ነው፡፡ ቤታችን በጋራ ጥረታችን የምትገነባ የሁላችን አለኝታ መሆኗን ለማስጨበጥና ውስጣዊ ሁኔታችን ደግሞ ይህን ለማድረግ ምቹ መሆኑን ለማስገንዘብ በተጨባጭም እውነታውን ለማሳየት ነው ቀኑ በየአመቱ እየተከበረ ያለው፡፡ በተግባርም በዓሉ እኛ ኢትዮጵያውያን የአስተሳሰብና የፖለቲካ ልዩነቶች ሳይገድቡን ይልቁንም በልዩነቶቻችን ውስጥ የምናሸበርቅባቸው ውብ እሴቶች ያሉንና ለአገራችን ብሔራዊ ጥቅም አንድ ላይ በመቆም የአገራችንን ህዳሴ ለማፋጠን ቆርጠን መነሳታችን ያሳየንበት በዓል ሆኖ አልፏል።

እስካሁን ያረጋገጥናቸው ዘርፈ ብዙ ስኬቶቻችን የኢትዮጵያ ጉዞ ብሩህና በተስፋ የተሞላ እንዲሆን ያስቻሉ ምስክሮች ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ እነዚያ በአገራችን የተመዘገቡ ሁለንተናዊ ስኬቶች በህዝቡ ያልተገደበ ተሳትፎ የተረጋገጡ ውጤቶች ናቸውና አሁንም በየትኛውም የዓለም ጫፍ ያለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ የራሱን አስተዋፅኦ በማበርከት የአገሩን ህዳሴ እውን ለማድረግ መረባረብ አለበት። እናም የጋራ ቤታችንን በጋር እንገንባ እላለሁ፡፡

No comments:

Post a Comment